ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
በትግራይ ያለው የጤና ሁኔታ ከየትኛውም የዓለም ክፍል በላይ አደጋ ላይ ነው፡ ዶ/ር ቴድሮስ
የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም በአሁኑ ወቅት ከየትኛውም የዓለማችን ክፍል በላይ የሰዎች ጤና አሳሳቢ ደረጃ ላይ የሚገኘው በትግራይ ክልል ውስጥ ነው አሉ።
ዋና ዳይሬክተሩ ትናንት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ፤ "በአሁኑ ወቅት ከየትኛውም የዓለማችን ክፍል በላይ በትግራይ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ጤና በአደጋ ላይ ይገኛል" ብለዋል።
"አዎ እኔ ከትግራይ ነኝ። ይህ ቀውስ እኔን፣ ቤተሰቤን እና ጓደኞቼን በግል ይጎዳል። ግን እንደ የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር፤ በስጋት ውስጥ ያለን ጤና የመጠበቅ እና የመንከባከብ ኃላፊነት አለብኝ። በአሁኑ ወቅት ከየትኛውም የዓለማችን ክፍል በላይ በትግራይ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን ጤና አሳሳቢ ደረጃ ላይ ይገኛል" ብለዋል።
ዋና ዳይሬክተሩ በክልሉ ላለው ሰብዓዊ ቀውስ የኢትዮጵያ እና የኤርትራ መንግሥታት ይፋዊ ያልሆነ እቀባን ተጠያቂ አድርገዋል።
የዋና ዳይሬክተሩን መግለጫ ተከትሎ ለኢትዮጵያ ዜና አገለግሎት (ኢዜአ) ምላሽ የሰጡት የመንግሥት ኮሙኒኬሽን ጽህፈት ኃላፊ ዶክተር ለገሠ ቱሉ ክሱ "ከእውነታው የራቀ እና መንግሥትን በሐሰት የወነጀለ ነው" ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።
ኃላፊው ጨምረውም "ህወሓት የእርዳታ መተላለፊያ ኮሪደሮችን መዝጋቱን ተከትሎ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አውሮፕላኖች በሳምንት ከሦስት ጊዜ በላይ ወደ ትግራይ እርዳታ እየተጓጓዘ መሆኑን" ተናግረዋል።
ጨምረውም "ህወሓት መንገድ በመዝጋት የህክምና ቁሳቁስና ሌሎች እርዳታዎች ወደ ትግራይ እንዳይደርስ እያደረገ መሆኑ እየታወቀ" ዋና ዳይሬክተሩ መንግሥትን ተወቃሽ ማድረጋቸው ትክክል አይደለም ብለዋል።
ዶ/ር ቴድሮስ በመግለጫቸው፤ ሩሲያ ከዩክሬን ጋር ሰላም እንድታወርድ ጥሪ እያቀረብን እንዳለነው ሁሉ፤ "ኢትዮጵያ እና ኤርትራ የጣሉትን ይፋዊ ያልሆነ እቀባ እንዲያነሱ እና ሕይወት ለማዳን የሰብዓዊ እርዳታ እንዲደርስ እንዲፈቅዱ ጥሪ እናቀርባለን" ብለዋል።
"95 ሜትሪክ ቶን መድኃኒት ወደ ትግራይ ለማድረስ ፍቃድ አላገኘንም"
ዶ/ር ቴድሮስ በመግለጫቸው የሚመሩት ድርጅት 95 ሺህ ሜትሪ ቶን መድኃኒት ወደ ትግራይ ለማድረስ ፍቃድ አለማግኘቱን ጨምረው ተናግረዋል።
ዶ/ር ቴድሮስ ላለፉት 500 ቀናት የኢትዮጵያ እና ኤርትራ መንግሥታት በትግራይ ያሉ 6 ሚሊዮን ሰዎችን ይፋዊ ባልሆነ እቀባ ሥር አድርገዋል ብለዋል።
የኢትዮጵያ መንግሥት በተደጋጋሚ በትግራይ ላይ ምንም አይነት እቀባ እንዳልጣለ ሲገልጽ መቆየቱ ይታወሳል።
በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እንደተናገሩት በአፋር በኩል የእርዳታ አቅርቦት ወደ ትግራይ እንዳይደርስ እንቅፋት የሆነው ህወሓት የሚያካሂደው ጥቃት እንደሆነ ገልጸው ነበር።
"ምንም ሊባል በሚችል ደረጃ ነዳጅ፣ ጥሬ ገንዘብ እና የግንኙነት መስመር የለም"
ከታኅሣሥ 2014 ዓ.ም. አጋማሽ ጀምሮ የምግብ እርዳታ ወደ ትግራይ እንዳልተላከ የተናገሩት ዶ/ር ቴድሮስ፤ ከአጠቃላይ ሕዝቡ 83 በመቶ የሚሆነው የምግብ ዋስትናው የተረጋገጠ አይደለም ብለዋል።
የዓለም ጤና ድርጅት ባደረገው ዳሰሳ በትግራይ ያሉ አንድ ሦስትኛ የሚሆኑት የጤና ተቋማት፤ "ተጎድተዋል አልያም ወድመዋል" ብለዋል ዳይሬክተር ጀነራሉ።
ከአንድ ወር በፊት የዓለም ጤና ድርጅት ለ300 ሺህ ሰዎች ሊበቃ የሚችል 33 ሜትሪክ ቶን መድኃኒት እና ሌሎች ግብዓቶችን ወደ ትግራይ በአየር ማደረሱን ተናግረዋል።
ባለፉት ሁለት ሳምንታትም ድርጅታቸው ከሌሎች አጋሮች ጋር በመሆን በትግራይ ለሚገኙ 65 የጤና ተቋማት ድጋፍ ማድረጉንም አመልክተዋል።
"ከዚህ በላይ ማድረግ ያስፈልጋል። ተጨማሪ 95 ሜትሪክ ቶን የጤና ግብዓት ለመላክ በዝግጅት ላይ ነን፤ ይሁን እንጂ እስካሁን ፍቃድ አላገኘንም" ብለዋል።
በትግራይ ለአስቿይ የጤና ችግሮች ምላሽ ለመስጠት 2ሺህ 200 ሜትሪክ ቶን የጤና ግብዓቶች ያስፈልጋሉ ያሉት ዶ/ር ቴድሮስ፤ እስካሁን ግን ማቅረብ የተቻለው 117 ሜትሪክ ቶን መሆኑን ተናግረዋል።
"ይህ ከሚፈለገው 1 በመቶ በታች ነው" በማለት የእርዳታ አቅርቦቱ መጠን እጅግ ያነሰ መሆኑን ገልጸዋል።
ዋና ዳይሬክተሩ በትግራይ ባለው የነዳጅ እጥረት በክልሉ የደረሱ የሰብዓዊ እርዳታ አቅርቦቶችን ወደሚፈለገው ቦታ ማድረስ "ከባድ ወይም የማይቻል" ያደርጎታል ብለዋል።
ዶ/ር ቴድሮስ ትናንት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ በአዋሳኝ አፋር ክልልም ያለው የሰብዓዊ ሁኔታ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየከፋ መምጣቱን ተናግረዋል።
በ10ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተፈናቅለው በሚገኙበት ሁኔታ፤ የምግብ፣ የመጠለያ እና የጤና አገልግሎት ያስፈልጋል ካሉ በኋላ፤ ከትግራይ ክልል ካለው ሁኔታ ጋር ሲነጻጸር አማራ እና አፋር ክልሎች የተሻለ ተደራሸ ናቸው ብለዋል።
"አጎራባች የሆኑት አፋር እና አማራ ቢጎዱም ከትግራይ በተሻለ ሁለቱ ክልሎች ተደራሽ ናቸው" ብለዋል የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር።
"የኤችአይቪ፣ የሳምባ፣ የካንሰር፣ የስኳር በሽተኞች ሕክምና እያገኙ አይደለም፤ እየሞቱም ሊሆን ይችላል።"
በነዳጅ እጥረት ምክንያት የዓለም ጤና ድርጅት አጋር ድርጅቶች የሥራ አድማሳቸውን ለማጥበብ መገደዳቸውን የሚናገሩት ዶ/ር ቴድሮስ፤ "በትግራይ ያለው ሁኔታ አስከፊ ነው። የኮሚዩኒኬሽን መስመር መዘጋት፣ ጋዜጠኞች ከትግራይ እንዳይዘጉ ማድረግ የተረሳ ቀውስ እንዲሆን ያደርገዋል" ብለዋል።
የኢትዮጵያ መንግሥት የኮሙኒኬሽን ኃላፊው ዶክተር ለገሠ የዓለም የጤና ድርጅት "በኢትዮጵያ በጦርነቱ የተጎዱ ሁሉንም አካባቢዎችን በፍትሃዊነት ከማገልገል ይልቅ ለአንድ አካባቢ ብቻ ትኩረት ሲያደርግ ይስተዋላል" በማለት ከድርጅቱ መርኅ ውጪ የሆነ ተግባር እየፈጸመ ነው ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል።
በሰሜን ኢትዮጵያ የተከሰተውን ጦርነት ተከትሎ የኢትዮጵያ መንግሥት የዓለም የጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር የሆኑት ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖምን ከሚመሩት ድርጅት መርኅ በተቃራኒ ወገንተኝነትን እያንጸባረቁ ነው በማለት በተደጋጋሚ ሲከሳቸው መቆየቱ ይታወሳል።