ኦሚክሮን፡ የዓለም ጤና ድርጅት በአዲሱ የኮሮናቫይረስ ዝርያ ምክንያት አገራት እንዳይደናገጡ አሳሳበ

የዓለም ጤና ድርጅት በአዲሱ የኮሮናቫይረስ ዝርያ ኦሚክሮን ምክንያት ዓለም መደናገጥ የለበትም ሲል አሳሳበ።

የቫይረሱ ዝርያ እንዳይስፋፋ ጥንቃቄ ማድረግ ነው እንጂ፤ መፍራት አያስፈልግም ብሏል ድርጅቱ።

አርብ ዕለት አንድ ኮንፍረንስ ላይ ንግግር ያደረጉት የዓለም ጤና ድርጅት ተመራማሪ ዶ/ር ሶዩምያ ሻሚናታን፤ አሁን ዓለም ያለችበት ሁኔታ አምና ከነበረው የተለየ ነው ብለዋል።

ኦሚክሮን እስካሁን ድረስ በ40 አገሮች ተገኝቷል። ዝርያው በክትባት አማካይነት የሚገታ ስለመሆኑ እስካሁን ግልጽ አይደለም።

ዶ/ር ሶዩምያ በደቡብ አፍሪካ የተሠራ ጥናትን አጣቅሰው "ይህ ዝርያ በከፍተኛ ሁኔታ ከሰው ወደ ሰው ይተላለፋል" ብለዋል።

"ለመገመት ከባድ ቢሆንም ዝርያው በዓለም የሚሰራጭ ሊሆን ይችላል። ለምሳሌ ዴልታ ዝርያ በዓለም ካሉ በበሽታው ከተያዙ ሰዎች 99 በመቶ ይሸፍናል" ሲሉም አክለዋል።

ዓለም ጭንቀት ውስጥ ከመግባት ይልቅ ጥንቃቄ ላይ ማተኮር እንዳለበት ባለሙያዋ አሳስበዋል።

የዓለም ጤና ድርጅት የድንገተኛ ጊዜ ኃላፊ ማይክ ራየን፤ አሁን ትኩረት መሰጠት ያለበት የኮሮናቫይረስ ክትባትን ማዳረስ ላይ እንደሆነ ተናግረዋል።

ክትባቱ የኦሚክሮን ዝርያን እንዲከላከል በሚል ማስተካከያ ሊደረግበት እንደሚገባ የሚጠቁም ጥናት እንደሌለ አስረድተዋል።

ኦሚክሮን መገኘቱን ተከትሎ አገራት በደቡብ አፍሪካ ላይ የበረራ እገዳ ጥለዋል።

አሜሪካ ወደ ግዛቷ የሚገቡ ተጓዦች ከበረራቸው አንድ ቀን አስቀድሞ የኮቪድ-19 ምርመራ እንዲያደርጉ መመሪያ ሰጥታለች።

በአሜሪካ የጉዞ ታሪክ የሌላቸው ሰዎች ላይም አዲሱ ዝርያ ተገኝቷል።

ሕንድም የ66 ዓመት ደቡብ አፍሪካዊ እና የ46 ዓመት ሕንዳዊ ሐኪም ላይ ዝርያውን ማግኘቷን አስታውቃለች።

የአውሮፓ አገራት የወረርሽኙን ዳግመኛ ስርጭት ለመቆጣጠር እየሞከሩ ባለበት ወቅት ነው አዲሱ ዝርያ የተከሰተው።

ጀርመን ያልተከተቡ ዜጎቿን ከመደብር፣ መዝናኛ እና ፊልም ቤት አግዳለች። ኦስትሪያ ደግሞ ክትባት መውሰድ ግዴታ ነው የሚል መመሪያ አውጥታለች።

ዩናይትድ ኪንግደም በበኩሏ 114 ሚሊዮን የፋይዘር እና ሞደርና ክትባቶች ገዝታለች። ጎልማሶች የኮሮናቫይረስ ክትባት ማጠናከሪያ (ቡስተር) ክትባት እንዲወስዱም እየገፋፋች ነው።