ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
በወር አበባ ምክንያት መምህሯ ያንጓጠጣት ተማሪ ራሷን አጠፋች
የ14 አመቷ ኬንያዊት ተማሪ የትምህርት ቤቷ ደንብ ልብስ በወር አበባ ርሶ ከታየ ከሰዓታት በኋላ ራሷን ማጥፋቷ ተሰምቷል።
እናቷ ቢያትሪስ ቺፕኩሩይ ልጇ ካቢያንጌክ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት በምትማርበት ወቅት አስተማሪዋ የደንብ ልብሷ ደም መራሱን ተመልክቶ አርብ ዕለት ከክፍል እንድትወጣ ብቻ ሳይሆን አንጓጥጧታል ይህ ከሆነ ከሰዓታት በኋላም ልጄን በሞት ተነጥቄያለሁ ብለዋል።
ይህንን ተከትሎም የልጅቷ ራሷን ማጥፋት ትክክለኛው ምክንያት መምህሩ መሆኑ አለመሆኑን ፖሊስ እያጣራሁ ነው ብሏል።
"የሴቶች ንፅህና መጠበቂያ ለመግዛት አቅሙ አልነበራትም። የወር አበባዋ ሲፈስ የተመለከተው አስተማሪ ግን ከክፍል አስወጥቶ ውጭ እንድትቆም አድርጓታል" በማለት እናት ይከስሳሉ።
ከናይሮቢ በምዕራብ በኩል 270 ኪ/ሜ በሚገኘው የሃገሪቱ ክፍል እናቷን ጨምሮ ከ200 በላይ ወላጆች መምህሩ እንዲታሰር ትናንት ተቃውሟቸውን አሰምተዋል።
ትምህርት ቤቱ በዚሁ ምክንያት የተዘጋ ሲሆን የተዘጋውን መንገድ ለማስከፈትም ፖሊስ አስለቃሽ ጋዝ ተኩሷል።
ከሁለት አመታት በፊት የወጣውን የኬንያ ሕግ ተከትሎ መንግሥት ለሁሉም የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች የንፅህና መጠበቂያ ለማቅረብ ወስኗል።
የሃገሪቱ የፓርላማ አባላት 4.5 ሚሊዮን ዶላር የሚያወጣው የተማሪዎቹ አመታዊ የንፅህና መጠበቂያ ፍጆታ በሚገባ በየትምህርት ቤቱ ስለመድረሱ እያጣሩ ይገኛሉ።