ፈረንሳይ፡ 17 ታካሚዎችን የመረዘው ዶክተር

ፈረንሳይ ውስጥ 17 ሰዎችን በመመረዝ የተጠረጠረው የህክምና ባለሙያ ምርመራ እየተደረገበት እንደሆነ ፖሊስ አስታወቀ።

ዶክተር ፍሬዴሪክ ፔሺዬ የማደንዘዣ ህክምና ባለሙያ ሲሆን፤ ከዚህ በፊትም ከሰባት ሰዎች መመረዝ ጋር በተያያዘ ምርመራ ሲደረግበት ነበር። በዚሁ ጉዳይ በአጠቃላይም 9 ሰዎች መሞታቸው ተገልጿል።

አቃቤ ሕግ ለፍርድ ቤት እንደገለጸው፤ ዶክተሩ ተግባሩን የፈጸመው በታካሚዎቹ ላይ ድንገተኛ ችግር የተከሰተ በማስመሰልና ባልደረቦቹ የሚጠቀሟቸው መሣሪያዎች ላይ ችግር በመፍጠር ችሎታውን ለማሳየት አስቦ ነው።

ዶክተር ፍሬዴሪክ ፔሺዬ ግን የቀረበበትን ክስ ሙሉ በሙሉ የካደ ሲሆን፤ ጥፋተኛ ሆኖ የሚገኝ ከሆነ እድሜ ልክ እስራት እንደሚጠብቀው ተገልጿል።

የዶክተሩ ጠበቃ ጆን ይቭስ ለ'ኤኤፍፒ' የዜና ምንጭ እንደገለጹት፤ ምርመራው ዶክተሩ ጥፋተኛ ስለመሆኑ አያረጋገረጥም።

''ዶክተሩ ታካሚዎችን እንደመረዘ ሊገምቱ ይችላል፤ ነገር ግን ይህ ግምት ብቻ ነው'' በማለት ተከራክረዋል።

የ47 ዓመቱ ፍሬዴሪክ ፔሺዬ በተመሳሳይ ክስ በአውሮፓውያኑ 2017 ፍርድ ቤት ቀርቦ የነበረ ሲሆን፤ ምንም ማስረጃ ባለመገኘቱ በነጻ ተሰናብቷል። ኋላ ላይ ግን የሥራ ፈቃዱ እንዲነጠቅ በፍርድ ቤት ተወስኖ ነበር።

ፖሊስ በዚህ ሳምንት 66 ሰዎች ያልታሰበ የልብ ድካም አጋጥሟቸው ነበር በማለት በድጋሚ ለጥያቄ ወስዶታል። በድጋሚ በቀረበበት ክስ መሰረትም እድሜያቸው ከአራት እስከ ሰማንያ የሚደርሱ ታካሚዎች በዶክተሩ ግዴለሽ አሰራር ጉዳት ደርሶባቸዋል።

ፍሬዴሪክ ፔሺዬ ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ '' የምርመራው ውጤት ምንም ይሁን ምን ሙያዬን አጥቻለሁ'' ብሏል።

''ከዚህ በኋላ ታካሚዎችን መርዟል የተባለ ዶክተርን ማን ሊያምን ይችላል? ቤተሰቦቼ በጣም አዝነዋል፤ ልጆቼ አንድ ነገር እንዳይሆኑም እሰጋለው" በማለት የደረሰበትን ጫና ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል።