ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ጀብድ የፈጸመው ተማሪ ጣልያናዊ ዜግነት ሊሰጠው ነው
ባለፈው ሳምንት በጣልያን 50 ተማሪዎችን አሳፍሮ የነበር የተማሪዎች አውቶቡስ ሾፌር መኪናውን ወዳልሆነ አቅጣጫ በመንዳት በመጨረሻም አውቶቡሱን በእሳት ሲለኩሰው የ13 ዓመቱ አዳጊ ራሚ ሺሃታ ደብቆ በያዘው ስልኩ ለፖሊስ ምልክት በመስጠት ጓደኞቹን ከሞት ማዳን ችሏል።
ስለዚህም አሁን የጣልያኑ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ሜቶ ሳልቪኒ ለግብጻዊው ራሚ የጣልያን ዜግነት እንዲሰጠው ፈቅደዋል።
የጣልያን ባለሥልጣናት ባለፈው ሳምንት ራሚ በፈጸመው ጀብድ ምክንያት ወዲኣውኑ ዜግነት ሊሰጡት ሲሉ የፀረ ስደተኛ አቋም ያለው ፓርቲ መሪ የሆኑት ሳልቪኒ ግን አንገራግረው ነበር።
ራሚ ምንም እንኳ ጣልያን ውስጥ ከግብፃዊ አባት ቢወለድም ጣልያን ከስደተኛ ለሚወለዱ ልጆች 18 ዓመት እስኪሆናቸው ድረስ ዜግነት ስለማትሰጥ ጣልያናዊ አልሆነም ነበር።
ሳልቪኒ ታዳጊው ላሳየው ጀግንነት ዜግነት እንደሚገባው ሲናገሩ፣ "አዎ ለራሚ ዜግነት ይሰጠዋል። ምክንያቱም ልክ እንደ ልጄ ስለሆነ እና የዚህን አገር እሴት እንደተረዳ ስላሳየን" በማለት ተናግረዋል።
ተማሪዎቹ የነበሩበት አውቶቡስ ውስጥ የነበረው ሌላው ሞሮካዊ ታዳጊ አዳም ኢል ሃማሚም ምንም እንኳ እሱም እንደ ራሚ በድብቅ ስለ አደጋው በስልኩ ለፖሊስ ጥሪ ቢያደርግም ለሱ ብዙ ትኩረት እየተሰጠው አይደለም።
ስለዚህም አባቱ ካሊድ ኢል ሃማሚ እንደ ራሚ ሁሉ ለልጃቸው አዳምም ዜግነት ሊሰጠው ይገባል ብለዋል። ሁሉም ስለ ራሚ ብቻ እያወራ በመሆኑም ልጃቸው እየተበሳጨ መሆኑንም አባቱ ተናግረዋል።
የጣልያን ባለሥልጣናት ግን አዳም የጣልያን ፓስፖርት ስለማግኘት አለማግኘቱ እስካሁን ያሉት ነገር የለም።