ያለአብራሪ በሚበረው የሰማይ ታክሲ ይጠቀማሉ?

የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች በሰውም ሆነ ያለሰው የሚበር የሰማይ ላይ ታክሲ ለገበያ ለማቅረብ እየተሯሯጡ ነው። ምን ያህል ይሳካላቸው ይሆን? እርስዎስ የሰማይ ላይ ታክሲዎቹን አምነው ይሳፈራሉ?

ዱባይ ደግሞ የሰማይ ላይ ታክሲዎቹን በመጠቀም ቀዳሚዋ ለመሆን እየሰራች ነው።

ባለፈው ሰኔ የዱባይ መንገድና ትራንስፖርት ባለስልጣን ቮሎኮፕተር ከተሰኘው የጀርመን ኩባንያ ጋር ሰው አልባ የሰማይ ላይ ታክሲዎችን ለመሞከር ከስምምነት ደርሷል።

ኩባንያው ሁለት ሰዎችን ማጓጓዝ የሚያስችል የሰማይ ላይ ታክሲ የመስራት ዕቅዱን እንዲያሳካ 25 ሚሊዮን ዩሮ ከባለሃብቶች አግኝቷል።

እንደድርጅቱ ከሆነ ታክሲው በሰዓት 100 ኪሎሜትር ይጓዛል። በሰማይ ላይ ለ30 ደቂቃ መቆየት የሚችል ሲሆን ለዚህም የሚረዱት ዘጠኝ ባትሪዎች ተገጥመውለታል።

"በአደጋ ወቅት የሚያስፈልገው ፓራሹት አስፈላጊ አይደለም" ሲል ቮሎኮፕተር ዋስትና ይሰጣል።

የዱባይ መንገድና ትራንስፐፖርት ባለስልጣን ከቻይናው ኤሃንግ ኩባንያ ጋር በመሆንም አንድ ሰው ማጓጓዝ የሚያስችለውን ኤሃንግ 184 የተሰኘ ድሮን (ሰው አልባ አነስተኛ አወሮፕላን) በመሞከር ላይ ይገኛል።

ሆኖም ዱባይ ያለሰው ከሚበሩት የሰማይ ላይ ታክሲዎችን ለመተግበር ከብዙ የዓለማችን ትልልቅ ከተሞች ጋር ከፍተኛ ፉክክር ውስጥ ገብታለች።

ኡበር የተሰኘው የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪ ተቋም የናሳውን ዋና የቴክኖሎጂ ባለሙያ ማርክ ሙርን ወደ ተቋሙ በመቀላቀል ፕሮጀክት ኢልቬት በተሸኘውና ወደፊት ለከተሞች በፍላጎት ላይ የተመሰረተ የትራንስፖርት ጥያቄን በሚፈታው ስራ ላይ መድቦታል።

የፈረንሳዩ አውሮፕላን አምራች ድርጅት ኤርባስ ከአውሮፕላኖቹ ጋር ተመሳሳይ የሆነ ቫሃና የተሰኘ የሰማይ ላይ ታክሲ በ2017 መጨረሻ ላይ የሚሞከር ሲሆን በ2020 ደግሞ ለገበያ ይቀርባል ተብሏል።

ተቋማቱ የመንገድ መዘጋጋት እየበዛ በመምጣቱ ፊታቸውን ወደ አየር ላይ እያዞሩ ነው። ለምሳሌ እንኳን በዓለማችን 10ኛዋ ሃብታም ከተማ ሳኦፖሎ በተለይ አርብ ዕለት መንገዶች ከ180 እስከ 295 ኪሎ ሜትር ድረስ ይዘጋጋሉ።

ኤሃንግ አንድ ተጓዥ፤ ቮሎኮፕተር ሁለት ሲቲ ኤርባስ ደግሞ ከአራት እስከ ስድስት ሰው የሚጭኑ የሰማይ ላይ ታክሲዎችን ለመስራት እያቀዱ ነው። ኩባንያዎቹ ታክሲዎቹን በኤሌክትሪክ እንዲሰሩ በማድረግ አካባቢ ላይ ጉዳት የማያደርሱ ለማድረግ እየጣሩ ነው።

ለመሆኑ እንዴት ይሰራሉ? በቀላሉስ ለመግዛት ይቻላል?

ሶስት ወይም አራት ሰው የሚይዘው የሰማይ ላይ ታክሲ ዋጋ 'ኡበር ኤክስ' ከተሰኘው የመኪና ዋጋ ጋር ተመሳሳይ መሆኑን ሙር ይገልጻል።

ያለውን ክብደትና ሃይል ከግምት በማስገባት እነዚህ ታክሲዎች ምን ያህል በአየር ላይ ይቆያሉ?

ሞባይልዎ ባትሪው እንዳይጨርስ የሚፈልጉትን ያህል የሰማይ በላይ ታክሲ ቢኖርዎትም ባትሪው እንዳያልቅ ይፈልጋሉ።

የቻይናው ኤሃንግ ድሮን ለ23 ደቂቃ መብረር ይችላል። ሆኖም የአሜሪካ አቪየሽን አስተዳደር ህግ አንድ አውሮፕላን ቢያንስ ለተጨማሪ 20 ደቂቃ የሚያቆውን ነዳጅ መያዝ አለበት። ይህ ማለት ደግሞ የኤሃንግ ድሮን መብረር የሚችለው ለሶስት ደቂቃ ብቻ ነው።

ኡበር 50 የሚሆኑ የሰማይ ላይ ታክሲዎቹን ለማውጣት ባቀደበት በ2023 ባትሪው ላይ ማሻሻያ በማድረግ ችግሩ ይፈታል ይላል ሙር።

ናሳ ያሻሻለው ቴክኖሎጂ ድሮኖች እርስ በእርስ የሚግባቡበትና ግጭት እንዳይኖር የሚረዳ ነው ተብሏል።

ዘርፉን ይበልጥ ወደ ኋላ የሚጎትተው የህግ ጉዳይ ነው ተብሏል።

በራሳቸው ተነስተው፥ በረው የሚያርፉ የንግድ አውሮፕላኖች ተግባራዊ ለመሆን ከጫፍ ቢደርሱም የአሜሪካ እና አውሮፓ የአቪየሺን ህጎች አውሮፕላኖች ያለአብራሪ እንዳይበሩ ያስገድዳሉ ሲሉ ፍራንኬል ዮኤል ይገልጻሉ።

ስለዚህ እነዚህ ድሮኖች ህግ የአውጪዎችን እምነት ለማግኘት ረዥም ጊዜ የሚወስድባቸው ይመስላል።

ዘርፉን ዱባይ እየመራቸው ሲሆን እንደ አስተዳዳሪዋ ሼክ መሃመድ ቢን ራሺድ አል ማክቱም ገለጻ ከሆነ በ2020 ከህዝብ ትራንስፖርት ውስጥ 25 በመቶው በራሱ የሚንቀሳቀስ የትራንስፖርት ዓይነት ይሆናል።

እንደአቪየሺን አማካሪው ማርክ ማርቲን ከሆነ ደግሞ "ንፋሳማው፥ አሸዋማውና ጉም ያለው የዱባይ አየር" ለድሮኖች አስቸጋሪ ነው።

ዱባይ በዘርፉ ላይ በፍጥነት እየሰራች ቢሆንም ከአሜሪካና አውሮፓ ህግ አውጪዎች ጋር ተቀራርባ መስራት ይጠበቅባታል ይላል።

"አንድ አደጋ ከደረሰ ከዛ በኋላ ማን አምኖ ድሮን ይጠቀማል?" ሲል ይጠይቃል።