ቢሊዮን ዶላሮች የሚያወጣ ቢትኮይን የዘረፈው አሜሪካዊ እስር ተፈረደበት

በዓለማችን እጅግ ግዙፍ ከሚባሉ የክሪፕቶከረንሲ ዝርፊያዎች በአንዱ የተፈፀመውን ገንዘብ አዘዋውሯል የተባለው አሜሪካዊ የአምስት ዓመት እስር ተፈረደበት።

ኢልያ ሊክችንስታይን ባለፈው ዓመት ነው ፍርድ ቤት ቀርቦ ጥፋተኛ መሆኑን ያመነው።

ቢትፋይኔክስ የተባለው የክሪፕቶከረንሲ መለዋወጫ መድረክ በአውሮፓውያኑ 2016 ተጠልፎ 120 ሺህ ቢትኮይን መዘረፉ ይታወሳል።

ግለሰቡ የተሰረቀውን ክሪፕቶ ያዘዋወረው ከሚስቱ ሄዘር ሞርጋን ጋር ሲሆን የሂፕ ሆፕ ሙዚቀኛዋ ሚስቱ ራዝልኻን በተሰኘ የመድረክ ስሟ ትታወቃለች።

ቢትኮይኑ በተሰረቀ ወቅት የገበያ ዋጋው 70 ሚሊዮን ዶላር ነበር። ነገር ግን በቁጥጥር ሥር ሲውሉ ዋጋው ተመንድጎ 4.5 ቢሊዮን ዶላር ደርሷል።

ግለሰቦቹ በቁጥጥር ሥር ሲውሉ 3.6 ቢሊዮን ዶላር ዋጋ ያለው ቢትኮይን ተይዞ ነበር።

በወቅቱ ምክትል አቃቤ ሕግ ሊሳ ሞናኮ በአሜሪካ የፍትሕ ሚኒስቴር ታሪክ ይህ ከፍተኛው በቁጥጥር ሥር የዋለ ገንዘብ ነው ማለታቸው አይዘነጋም።

“እንዲህ ዓይነት ወንጀል ፈፅመው ሳይቀጡ እንደማያልፉ ማሳያ ነው። የሚፈፅሙት እያንዳንዱ ወንጀል መዘዝ አለው” ሲሉ ዳኛ ኮሊን ኮላር-ኮቴሊ ተናግረዋል።

ሊክችንስታይን በአውሮፓውያኑ የካቲት 2022 ነው በቁጥጥር ሥር ውሎ እስር ቤት የገባው። ሰውዬው በፈፀመው ወንጀል መፀፀቱን ለችሎቱ ተናግሯል።

አክሎ እስሩን ጨርሶ ሲወጣ ችሎታውን ተጠቅሞ የሳይበር ወንጀለኞችን ለመከላከል እንደሚሠራ ቃል ገብቷል።

ሚስቱ ሞርጋን በገንዘብ ማዘዋወር ውስጥ እጇ እንዳለበት አምና ጥፋተኛ ነው ያለችው ባለፈው ዓመት ነው። በሚቀጥለው ሳምንት ሰኞ ፍርድ ቤት ቀርቦ ብይን ይሰጣታል ተብሎ ይጠበቃል።

የፍርድ ቤት መዛግብት እንደሚያሳዩት ሊክችንስታይን የረቀቀ ቴክኖሎጂ በመጠቀም ነው የድርጅቱ ‘ሲስተም’ ውስጥ ገብቶ ገንዘቡን ያዋወረው።

ገንዘቡን ከዘረፈ በኋላ ከሚስቱ ጋር በመሆኑ የተለያዩ ውስብስብ የሆኑ መንገዶችን ተጠቅሞ ሲያዘዋውር ቆይቷል የፍትሕ ሚኒስቴር መግለጫ።

ግለሰቡ እና ሚስቱ ከተጠቀሟቸው መላዎች መካከል የተፈበረከ ማንነት፣ ገንዘቡን ወደተለያዩ ክሪፕቶከረንሲዎች ማዛወር እና የወርቅ ሳንቲሞችን መግዛት ይገኙበታል።

ሊክችንስታይን ሩሲያ ተወልዶ አሜሪካ ያደገ ሲሆን ከቤተሰብ ጋር ለጉብኝት በሄደበት ወቅት ገንዘቡን የሚያዘዋውሩለት ሰዎች አግኝቶ እንደነበር አቃቤ ሕግ ተናግሯል።

ጥንዶቹ በቁጥጥር ሥር ሲውሉ ራዝልኻን በተሰኘው የሂፕ ሆፕ ስሟ የምትታወቀው ሞርጋን ስሟ በማኅበራዊ ሚድያ ከፍተኛ መነጋጋሪያ ሆኖ ነበር።

በሂፕ ሆፕ ዘፈኖቿ የቪድዮ ክሊፕ ላይ ራሷን “ከባድ ገንዘብ ሠሪ” እና “የዎል ስትሪት አዞ” ስትል ታሞካሻለች።