የሱዳን ተቃውሞ፡ የሟቾች ቁጥር 100 መድረሱን ተቃዋሚዎች እያስታወቁ ነው

የሱዳን ደኀንነት ኃይሎች በዋና ከተማዋ ካርቱምና በጦር ኃይሉ ዋና መሥሪያ ቤት ተሰማርተዋል

የፎቶው ባለመብት, AFP

የምስሉ መግለጫ, የሱዳን ደኀንነት ኃይሎች በዋና ከተማዋ ካርቱምና በጦር ኃይሉ ዋና መሥሪያ ቤት ተሰማርተዋል

በሱዳን የተቃውሞ ሰልፉን የሚመሩ አክቲቪስቶች በዋና ከተማዋ ካርቱም በወታደሮች የተገደሉ ሰልፈኞች አስክሬን ከናይል ወንዝ ውስጥ እየወጣ መሆኑን ተናግረዋል።

ዛሬ ማለዳ የተቃዋሚ ዶክተሮች ስብስብ የሆነ አንድ ማሕበር በሱዳን ተቃውሞ የሞቱ ሰዎቸ ቁጥር 60 መድረሱን አስታውቆ ነበር። ከሰኞ እለት ጀምሮ በወታደሮች የተገደሉ ተቃዋሚ ሰልፈኞች አንድ መቶ መድረሱ የተዘገበው ዛሬ ከሰአት በኋላ ነው።

የሚሊሻ አባላቱ ንፁሐንን በመግደል ተጠርጥረዋል።

ከሰኞ ጀምሮ ተቃውሞ እንደ አዲስ የበረታባት ካርቱም የሰላም እንቅልፍ ሳታሸልብ ሁለት ቀን ኦልፏታል።

ጊዜያዊው ወታደራዊ መንግሥት ሥልጣን ለሲቪል ያስረክብ ያሉ ተቃዋሚዎች ጋር ግጭት ውስጥ የገባው ነውጠኛው የሚሊሻ ቡድን የሰው ሕይወት አጥፍቷል ሲሉ ተቃዋሚዎች ይወነጅላሉ።

የወታደራዊ ኃይል ቡድኑ ዓለም አቀፍ ጫና የበረታበት ይመስላል። እንግሊዝ እና ጀርመን የተባበሩት መንግሥታት ወታደራዊው ጊዜያዊ መንግሥት መፍትሄ ያበጅ ዘንድ ተማፅነዋል፤ ቻይና እና ሩስያ በሱዳን ጉዳይ እያሤሩ ነው ሲሉም ወቅሰዋል።

የሱዳን መከላከያ ኃይል ዋና መሥሪያ ቤት ደጃፍ ሲደረግ የነበረው የመቀመጥ አድማ ለወራት የዘለቀ ቢሆንም ዕለተ ሰኞ የሆነው ግን ተቃዋሚዎች ያልጠበቁት ነበር። የሱዳን ልዩ ኃይል በአስለቃሽ ጋዝ በመታገዝ ሰልፈኞችን ይበታትን ያዘ።

ሱዳናውያን በአል-ባሽር ዘመን ጃንጃዊድ በሚል ስያሜ የሚታወቀው ልዩ ኃይሉ ሰላማዊ ዜጎች ላይ የተጠና እርምጃ ወስዷል ሲሉ ይከሳሉ።

ጊዜያዊው ወታደራዊ አገዛዝ በዘጠኝ ወራት ጊዜ ውስጥ ምርጫ ይካሄዳል የሚል መግለጫ ቢያወጣም ሱዳናውያን የአል-በሽር ሽታ ያልለቀቃቸውን ሰዎች ለማፅዳት ረዘም ያለ ጊዜ ያሻል ሲሉ ይሞግታሉ።

ወታደራዊው መንግሥት እና የነፃነትና የለውጥ ኃይል የተሰኘው ተቃዋሚ ቡድን ደርሰውት የነበረውን ስምምነት ጊዜያዊው አስተዳደር አፍርሶታል ይላል የቢቢሲ አፍሪቃው ተንታኝ ፈርጋል ኪን።

የሱዳን ተቃውሞ፡ የሟቾች ቁጥር 60 ደርሷል

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

አክሎም ወታደራዊው መንግሥት ከዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ ብርቱ ጫና እየደረሰበት አይደለም ባይ ነው ተንታኙ። በዚህ የክፍፍል ዘመን ጫና ሁሉም ተባብረው ጫና ያደርሳሉ ማለት ዘበት ነው ይላል ኪን።

ወጣም ወረደ ሱዳናውያን የረመዳን ፆምን ከሚቃጠል ጎማ በሚወጣ ጭሥ ታጅበው፤ ሠላም እንደራቃቸው አሳልፈዋል፤ ፆሙንም የፈቱት አደባባይ ላይ ሆነው ነው።

ማሕበራዊ ድር አምባዎች ላይ የሚለቀቁ ምስሎች የሱዳን ወታደሮች መንገዶችን እንደተቆጣጠሩት የሚያሳዩ ናቸው።

ጥርስ አልባ እንበሳ እየተባለ የሚታማው የተመባበሩት መንግሥታት ወታደራዊው መንግሥት መፍትሄ እንዲያበጅ ከመማፀን ወደኋላ አላለም።