ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
መንግሥት እርዳታ ለማቅረብ ወደ ትግራይ የሚደረጉ በረራዎችን ፈቀደ
የፌደራሉ መንግሥት የሰብዓዊ እርዳታ ማቅረብ ለሚሹ ሁሉም አካል ወደ ትግራይ በረራ እንዲያደርጉ መፍቀዱን አስታወቀ።
የአስቸኳይ ጊዜ መረጃ ማጣሪያ በትዊተር ገጹ ይፋ እንዳደረገው የፌደራሉ መንግሥት ወደ ትግራይ የሚደረጉ በረራዎች ከሰኞ ሰኔ 28/ 2013 ዓ.ም ጀምሮ ፍቃድ መሰጠቱን ይፋ አድርጓል።
ይሁን እንጂ መንግሥት የሰጠው የበረራ ፍቃድ፤ ከዓለም አቀፍ መነሻዎች በቀጥታ ወደ ትግራይ ለሚደረጉ የቀጥታ በረራዎች ይሁን አልያም በሌሎች የአገሪቱ ክፍሎች ከሚገኙ የአየር ማረፊያዎች ወደ ትግራይ ክልል ስለሚደረጉ በረራዎች ስለመሆኑ ግልጽ የሆነ ነገር የለም።
የፌደራሉ መንግሥት የተናጠል የተኩስ አቁም ማወጁን ተከትሎ የህወሓት ኃይሎች በተመሳሳይ የተኩስ አቁም ለማድረግ ባለ ሰባት ነጥብ ቅድመ ሁኔታዎችን ባለፈው ዕሁድ ለፌደራሉ መንግሥቱ ማቅረባቸው ይታወሳል።
ከእነዚህ ቅድመ ሁኔታዎች መካከል "ያለ ቅድመ ሁኔታ ዓለም አቀፍ በረራዎች በትግራይ ወደሚገኙ አየር ማረፊያዎች የቀጥታ ጉዞ እንዲያደርጉ መፈቀድ" የሚል ተካቷል።
በትግራይ ኃይሎች እና በፌደራል መንግሥቱ መካከል በተቀሰቀሰው ግጭት በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች አስቸኳይ የሰብዓዊ እርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው ምዕራባውያን አገራት እና የተራድኦ ድርጅቶች ሲያሳውቁ ቆይተዋል።
ምዕራባውያኑ የሰብዓዊ እርዳታ ለሚያስፈልጋቸው ድጋፍ ለማድረሰም እንቅስቃሴያቸው ሳይገደብ ድጋፍ ማድረግ እንዲቻላቸው ሲጠይቁ ቆይተዋል።
ባለፈው ሳምንት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ባወጣው መረጃ በአሁኑ ጊዜ በትግራይ ክልል ውስጥ 400 ሺህ የሚሆኑ ሰዎች በረሃብ ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኙ አስጠንቅቆ ነበር።