እነ አቶ ጃዋር የረሃብ አድማ እንዲያቆሙ በሃይማኖት አባቶች እና ፖለቲከኞች ተጠይቀው ፍቃደኛ ሳይሆኑ ቀሩ

የፎቶው ባለመብት, Kamil Shemsu
ከ12 ቀናት በላይ በረሃብ አድማ ላይ የሚገኙት እነ አቶ ጃዋር መሐመድ የረሃብ አድማውን እንዲያቆሙ በሃይማኖት አባቶች እና ፖለቲከኞች ቢጠየቁም ፍቃደኛ ሳይሆኑ ቀሩ።
ከድምጻዊ ሃጫሉ በኋላ በቁጥጥር ስር ዋሉት እና ክስ ተመስርቶባቸው በእስር የሚገኙት እነ አቶ ጃዋር መሐመድ፣ በቀለ ገርባ፣ ሸመሰዲን ጠሃ እና ሃምዛ አዳነ በፖለቲከኞች እና በቤተሰብ አባላቶቻቸው ላይ የሚደርሰውን እስር እና ወከባ በመቃወም የረሃብ አድማ ማድረግ ከጀመሩ 12 ቀን አልፏቸዋል።
ከአራቱ ተከሳሾች በተጨማሪ በአቶ ጃዋር መሐመድ የክስ መዝገብ ሥር የሚገኙት የአቶ ጃዋር መሐመድ ጠባቂዎች እና የኦሮሚያ ሚዲያ ኔትዎርክ ጋዜጠኛ መለሰ ዲሪብሳ የረሃብ አድማውን ተቀላቅለዋል።
ከእነ አቶ ጃዋር ጠበቆች መካከል አንዱ የሆኑት አቶ ከድር ቡሎ ለቢቢሲ እንደተናገሩት ከዚህ ቀደም ጠበቆች እና የቤተሰብ አባላት ምግብ እንዲበሉ ሲጠይቋቸው ቢቆዩም ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል።
ዛሬ ታዋቂ ፖለቲከኞች እና የሃይማኖት አባቶች ቃሊቲ ማረሚያ ቤት ተገኝተው ተከሳሾች የረሃብ አድማቸውን እንዲያቆሙ ቢጠይቋቸውም ፈቃደኛ ሳይሆኑ መቅረታቸውን አቶ ከድር ለቢቢሲ ተናግረዋል።
"ከፖለቲከኞች የኦነግ ሊቀመንበር አቶ ዳውድ ኢብሳ፣ አቶ ሌንጮ ለታ፣ አቶ ባቴ ኡርጌሳ፣ ከሃይማኖት አባቶች ደግሞ ኡስታዝ ካሚል ሸምሱ ቃሊቲ ተገኝተው ቢለምኗቸውም ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል"
ሌላኛው የእነ አቶ ጃዋር ጠበቃ አቶ ሙስጋኑ ሙለታ፤ ፖለቲከኞቹ እና የሃይማኖት አባቶች የረሃብ አድማውን እንዲያቆሙ ሲጠይቁ በስፍራው እንደነበሩ ይናገራሉ።
"እነ አቶ ጃዋር በጣም ተዳክመዋል። ብዙ መናገር እና መራመድ አይችሉም። ሰውነታቸው ዝሏል። ሃኪሞችም ብዙ አታውሩ ብለዋቸዋል" ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል።
"ለሽምግልና የሄዱት ሰዎች 'ምግብ ብሉ። በራሳችሁ ላይ ጉዳት አታደርሱ' ሲሉ ነበር የጠየቋቸው። ይሁን እንጂ ፍቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል" ሲሉ አቶ ምስጋኑ ተናግረዋል።
አቶ ከድር ቡሎ በበኩላቸው የረሃብ አድማ እያደረጉ ካሉ ተከሳሾች መካከል የሕክምና እርዳታ አስፈልጓቸው ወደ ጤና ተቋም እየተወሰዱ ያሉ ተከሳሾች መኖራቸውን ተናግረዋል።
ባሳለፍነው እሁድ የእነ አቶ ጃዋር መሐመድ ሃኪሞች "ምርመራ ካደረጉላቸው በኋላ ውሃ ካልወሰዱ አንዳንድ የሰውነት አካላቸው ሥራ ሊያቆም እንደሚችል ከነገሯቸው በኋላ ነው በግድ ውሃ እየወሰዱ ነው ያሉት። ምግብ የሚባል ነገር አፋቸው ጋር እየደረሰ አይደለም" ሲሉ ከእነ አቶ ጃዋር ጠበቆች መካከል አንዱ የሆኑት ምስጋኑ ሙለታ ለቢቢሲ ተናግረው ነበር።
የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በቁጥጥር ሥር የዋሉት እነ አቶ ጃዋር ከቀረቡባቸው ተደራራቢ አስር ክሶች ስድስቱ እንዲቋረጡ ፍርድ መወሰኑ ይታወሳል።
የሽብር ወንጀልን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር የወጣውን አዋጅ፤ የቴሌኮም ማጭበርበር ወንጀል አዋጅ ፤ የጦር መሳሪያ አስተዳደርና ቁጥጥር አዋጅ የመተላለፍ ክሶች ከተመሰረቱባቸው ክሶች መካከል ሲሆኑ፤ እንዲቋረጡ የተደረጉት ክሶች የጦር መሳሪያ አስተዳደር እና ቁጥጥር አዋጅ 1177/2021 ጋር የተያያዙ ናቸው።
የረሃብ አድማ ለምን?
እነ አቶ ጃዋር መሐመድ የረሃብ አድማውን እያደረጉ ያሉት በፖለቲከኞች ላይ የሚደርሰውን እንግልት እና እስር፣ እነሱን ለመጠየቅና የችሎት ሂደታቸውን ለመከታተል ወደ ፍርድ ቤት በሚመጡ ሰዎች ላይ የሚፈጸም እስር እና ወከባ እንዲቆም ለመጠየቅ ነው።
እነ አቶ ጃዋር መሐመድ እና በቀለ ገርባን ጨምሮ በርካታ ፖለቲከኞች የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያን ተከትሎ ከተፈጠረው ሁከት ጋር ተያይዞ እጃችሁ አለበት ተብለው ተጠርጥረው በቁጥጥር ሥር መዋላቸው የሚታወስ ነው።
ከእነ አቶ ጃዋር በተጨማሪ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር ከፍተኛ አመራሮች በተመሳሳይ የረሃብ አድማ ላይ ይገኛሉ። አቶ ሚካኤል ቦረን እና ኬነሳ አያና ፍርድ ቤት የዋስትና መብታቸው ተከብሮ ጉዳያቸው ከውጪ ሆነው እንዲከታተሉ ቢፈቅድላቸውም ፖሊስ እስረኞቹን አልለቅም በማለቱ የረሃብ አድማ ላይ እንደሚገኙ ጠበቃቸው አቶ ቱሊ ባይሳ ለቢቢሲ ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ኮሚሽነር ዳንኤል በቀለ (ዶ/ር) የረሃብ አድማው ተከሳሾችን የከፋ አደጋ ላይ እንዳይጥል የቅርብ ክትትል ማድረግ እንደሚያስፈልግ መግለጻቸውን ኮሚሽኑ ባሳለፍነው አርብ ባወጣው መግለጫ አስነብቧል።
"ለታሳሪዎች ምክንያታዊ የሆኑ ጥያቄዎች ተገቢውን አፋጣኝ ምላሽ መስጠትና የእስረኞችን ጠያቂዎች በማረሚያ ቤቱም ሆነ በፍርድ ቤቶች በአግባቡ ማስተናገድ ይገባል" ስለማለታቸው በመግለጫው ሰፍሯል።














