ቀጥታ, የኢራን የተኩስ አቁም “በቋፍ ላይ” መሆኑን ትራምፕ ተናገሩ

የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኢራን የተኩስ አቁም ስምምነት “በማይታመን ሁኔታ ደካማ” መሆኑን ተናገሩ። ፕሬዝዳንቱ ትናንት ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት፤ አንድ ወር ያስቆጠረው የተኩስ አቁም ስምምነት “በሕይወት ለመቆየት እየተንገዳገደ” ይገኛል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ኢራን ጥቃት ከደረሰባት መሣሪያ መገንባት በሚያስችል መጠን ዩራኒየም ለማበልጸግ ዛተች

    ኢራን በድጋሚ ጥቃት የሚፈጸምባት ከሆነ መሣሪያ ለመገንባት በሚያስችል የጥራት መጠን ዩራኒየም ማበልጸግ እንደምትጀምር ማስታወቋን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘገበ።

    በኢራን ምክር ቤት ንግግር ያደረጉት የብሔራዊ ደኅንነት እና የውጭ ጉዳይ ኮሚቴ ቃል አቀባይ ኢብራሒም ራይዚ፤ ኢራን ጥቃት ከደረሰባት ዩራኒየም በ90 በመቶ ደረጃ እንደምታበለጽግ አስታውቀዋል።

    ቃል አቀባዩ በኤክስ ገጻቸው “ኢራን ሌላ ጥቃት ከተፈጸመባት እስከ 90 በመቶ ማበልጸግን አንድ አማራጭ አድርጋ ትወስዳለች። ጉዳዩን በምክር ቤት እንወያይበታለን” ብለዋል።

  2. የኢራንን ነዳጅ ለቻይና ሸጠዋል የተባሉ 12 ግለሰቦች እና ተቋማት በአሜሪካ ማዕቀብ ተጣለባቸው

    የአሜሪካ ግምጃ ቤት የኢራንን ነዳጅ ለቻይና የሸጡ ወይም ያዘዋወሩ ናቸው ባላቸው 12 ግለሰቦች እና ተቋማት ላይ ማዕቀብ መጣሉን አስታወቀ።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ በፈጠራቸው ወረቀት ላይ ብቻ የሚገኙ ኩባንያዎች (shell companies) አማካኝነት በድብቅ የነዳጅ ሽያጭ እንደሚያከናውን ተገልጿል።

    ብዙም ቁጥጥር በማይደረግባቸው ዘርፎች ውስጥ የሚፈጠሩት እነዚህ የይስሙላ ኩባንያዎች ነዳጅ እየሸጡ ለኢራን መንግሥት ገቢ እንደሚያስገኙ የአሜሪካ ግምጃ ቤት አስታውቋል።

    ከነዳጅ ሽያጭ የሚገኘው ገቢ ለጦር መሣሪያ ምርት እና ኢራንን በእጅ አዙር ለሚደግፉ የውጭ አገራት ቡድኖች እንደሚውል ገልጿል።

    የአሜሪካ የግምጃ ቤት ጸሐፊ ስኮት ቤሴት “የኢራን ወታደራዊ ኃይሎች አቅማቸውን ለመገንባት እየሞከሩ ነው። እኛም የምጣኔ ሃብት ጫና ማሳደር እንቀጥላለን” ሲሉ በኤክስ ገጻቸው ጽፈዋል።

    “የኢራን መንግሥት የፋይናንስ ምንጮችን እንዘጋለን። የሽብር ድርጊቶችን በመደገፍ ዓለም አቀፍ ምጣኔ ሃብትን የሚያናጉበትን ትስስርም እንበጣጥሳለን” ሲሉም አክለዋል።

  3. “የኢራናውያንን መብት ከማክበር ውጪ አሜሪካ ሌላ አማራጭ የላትም” አፈ ጉባኤ ጋሊባፍ

    ሞሐመድ ባጊር ጋሊባፍ
    የምስሉ መግለጫ, አፈ ጉባኤ ሞሐመድ ባጊር ጋሊባፍ

    ከስምምነት ላይ ለመድረስ አሜሪካ የኢራናውያንን መብት ከማክበር ውጪ ሌላ አማራጭ የላትም ሲሉ በአገሪቱ ውስጥ ከፍተኛ ተሰሚነት ያላቸው የኢራን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ገለጹ።

    አፈ ጉባኤው መሐመድ ባጊር ጋሊባፍ ለፕሬዝዳንት ትራምፕ አስተያየት ምላሽ በኤክስ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሁፍ እንዳሉት ኢራን ጦርነቱን ለማስቆም ባቀረበችው “ባለ14 ነጥብ ሃሳብ ላይ እንደተቀመጠው የኢራናውያንን መብቶች ከማክበር ውጪ ሌላ ምንም አማራጭ የለም” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ጦርነቱን ለማስቆም ከኢራን በኩል በተሰጠው ምላሽ ደስተኛ አለመሆናቸውን በተመለከተ ሰኞ ዕለት የተኩስ አቁሙ “በቋፍ ላይ” መሆኑን ከተናገሩ በኋላ ነው አፈ ጉባኤው በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የአገራቸውን አቋም ያስታወቁት።

    ጋሊባፍ በኤክስ ገጻቸው ላይ በእንግሊዝኛ እንደጻፉት “ሌላ የትኛውም መንገድ ተከታታይ ውድቀትን ከማስከተል ውጪ ምንም ዓይነት ውጤትን አያስገኝም። ነገሩ እየተራዘመ ሲሄድ ከአሜሪካውያን ታክስ ከፋዮች ኪስ የሚወጣውን ወጪን ይጨምራል” በማለት አሳስበዋል።

    የኢራን ምክር ቤት አፈጉበኤ ጋሊባፍ ከዚህ ቀደም ብሎ ባሠራጩት የማኅበራዊ ሚዲያ መልዕክት ኢራን ለየትኘውም ሁኔታ ዝግጁ መሆኗን አስታውቀው ነበር።

  4. የኢራን ተኩስ አቁም “በቋፍ ላይ” መሆኑን ትራምፕ ተናገሩ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኢራን የተኩስ አቁም ስምምነት “በቋፍ ላይ” እንደሚገኝ ተናገሩ። የተኩስ አቁሙ ዘላቂነት “በማይታመን ሁኔታ ደካማ” መሆኑንም ገልጸዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ትናንት ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት፤ አንድ ወር ያስቆጠረው የተኩስ አቁም ስምምነት “በሕይወት ለመቆየት እየተንገዳገደ” ይገኛል።

    የትራምፕን አስተያየት ተከትሎ የኢራን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ መሐማድ ጋሊባፍ “ለማንኛውም ወረራ ምላሽ ለመስጠት እና ትምህርት ለማስተማር ዝግጁ ነን” ብለው በኤክስ ገጻቸው ምላሽ ሰጥተዋል።

    አሜሪካ ለኢራን ላቀረበችው የሰላም ዕቅድ ቴህራን የሰጠችው ምላሽ በዋሽንግተን ውድቅ ተደርጓል።

    ያለፈው እሑድ ኢራን ጦርነቱን ለማስቆም እና የሆርሙዝ ወሽመጥን ለመክፈት ለአሜሪካ ያቀረበችው ዕቅድ ተቀባይነት አላገኘም። ፕሬዝዳንቱም “ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለው” እና “ቆሻሻ” ሲሉ ዕቅዱን አጣጥለዋል።

    ትራምፕ ይህንን ካሉ በኋላ የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢስማኤል ባጊ የቴህራን ዕቅድ “ኃላፊነት የተሞላው” እና “ቸር” መሆኑን ተናግረዋል።

    የኢራን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ “በ14ቱ ነጥቦች እንደተመለከተው የኢራናውያንን መብት ከማክበር ውጭ አማራጭ የለም። ሳይቀበሉት በዘገዩ ቁጥር የአሜሪካውያን ግብር ከፋዮች ገንዘብ ይባክናል” ብለዋል።

    በኢራን እና አሜሪካ መካከል የተወሰኑ ግጭቶች ቢኖሩም የተኩስ አቁም ስምምነቱ አንድ ወር አስቆጥሯል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ፤ “የተኩስ አቁም ስምምነቱ በሕክምና እርዳታ እንደሚተነፍስ ታማሚ ነው። ሐኪሞች መጥተው ‘ጌታዬ የሚወዱት ሰው በሕይወት የመቆየት ዕድሉ 1 በመቶ ነው’ የሚሉት ዓይነት ነው” ብለዋል።

  5. ሆርሙዝ በጥቂት ሳምንታት ውስጥ ካልተከፈተ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች ለረሃብ ይጋለጣሉ ተባለ

    ማዳበሪያ የሚበትን ሰው

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በሆርሙዝ ወሽመጥ መዘጋት የአፈር ማዳበሪያ አቅርቦት ተስተጓጉሏል

    የሆርሙዝ ወሽመጥ በቶሎ ተከፍቶ የማዳበሪያ ምርት በባሕረ ሰላጤው መተላለፍ ካልቻለ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች የምግብ እጥረት እና ረሃብ እንደሚገጥማቸው አንድ የተበባሩት መንግሥታት ባለሥልጣን ተናገሩ።

    ባለሥልጣኑ ለፈረንሳይ የዜና ወኪል ኤኤፍፒ እንደተናገሩት ወራት ባስቆጠረው የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ምክንያት በሆርሙዝ በኩል የሚደረገው የመርከቦች እንቅስቃሴ መስተጓጎሉ ለእርሻ ምርት አስፈላጊ የሆነውን የአፈር ማዳበሪያ አቅርቦት አደናቅፎታል።

    ስለዚህም በጥቂት ሳምንታት ውስጥ የሆርሙዝ ወሽመጥ ተከፍቶ የአፈር ማዳበሪያ ምርት እና ግብዓት እንዲያልፍ ካልተፈቀደ የምግብ ምርት መስተጓጎል እና ረሃብ ሊያስከትል እንደሚችል የመንግሥታቱ ድርጅት የፕሮጀክቶች ጽህፈት ቤት ኃላፊ የሆኑት ዮርግ ዳ ሲልቫ ተናግረዋል።

    ባለሥልጣኑ "ከፍተኛ የሰብአዊ ቀውስ ሊሆን የሚችለውን ችግር ለመቀልበስ ያሉን ጥቂት ሳምንታት ብቻ ናቸው” ሲሉ ለዜና ወኪሉ ገልጸዋል።

    አክለውም በጦርነቱ ሰበብ የአፈር ማዳበሪያ ምርቱ አቅርቦት በመስተጓጎሉ "ተጨማሪ 45 ሚሊዮን የሚሆኑ ተጨማሪ ሰዎችን ለምግብ እጥረት እና ለረሃብ የሚዳርግ ቀውስ ሊገጥመን ይችላል” ብለዋል።

    ባለፈው የካቲት ወር ማብቂያ አካባቢ በተቀሰቀሰው ጦርነት ምክንያት ኢራን እና አሜሪካ በወሳኙ የባሕር መተለላፊያ የሆርሙዝ ወሽመጥ የጭነት መርከቦች እንዳይንቀሳቀሱ የሚያደርግ እገዳ ጥለዋል።

    ካርታ
  6. ስለ አሜሪካ የጦር መሣሪያ ክምችት የተናገሩት ሴናተር ምርመራ እንደሚደረግባቸው መከላከያ ሚኒስትሩ ገለጹ

    ዴሞክራቱ ሴናተር ማርክ ኬሊ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት፣ መሥሪያ ቤታቸው ዴሞክራቱ ሴናተር ማርክ ኬሊ ስለ አገሪቱ የጦር መሣሪያ ክምችት የሰጡትን አስተያየት እንዲመረምር ጠየቁ።

    ሴናተሩ “ቴሌቪዥን ላይ” ቀርበው ምሥጢራዊ ስለሆነ የፔንታጎን መረጃ “ዘላብደዋል” ያሉት ሄግሴት፤ "በድጋሚ... መሐላውን ጥሷል?" ሲሉ ኤክስ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሑፍ ጠይቀዋል።

    ሴናተሩ ኬሪ ወቀሳ ያስነሳባቸውን ንግግር ያደረጉት ከሲቢኤስ ኒውስ ‘ፌስ ዘ ኔሽን’ ፕሮግራም ጋር በነበራቸው ቆይታ ነው። ፕሮግራሙ ላይ ቀርበው በኢራን ጦርነት ምክንያት ስለ አሜሪካ የጦር መሣሪያ ክምችት የተሰማቸው ስጋት ገልጸው ነበር።

    የጦር መሣሪያዎችን የሚዘረዝር የፔንታጎን ማብራሪያም በማጣቀስ የመሣሪያ ክምችቱ ምን ጥቅም ላይ እንደዋለ መረዳታቸው “አስደንጋጭ” እንደሆነ ተናግረዋል።

    ኬሊ፤ ከዚህ ቃለ መጠይቅ በኋላ ከመከላከያ ሚኒስትሩ ለቀረበባቸው ክስ በሰጡት ምላሽ ምሥጢራዊ መረጃ አውጥተዋል መባሉን አስተባብለዋል። ስለዚህ ጉዳይ “ከሳምንት በፊት ይፋዊ ውይይት ላይ ተነጋግረናል” ሲሉ ጉዳዩ ምሥጢር እንዳልነበረ ተከራክረዋል።

    የአሪዞናው ሴናተር በኤክስ ገጻቸው በሰጡት ምላሽ፤ "ከእነዚህ ክምችቶች የተወሰኑትን ወደ ነበሩበት ለመመለስ 'ዓመታት' ተናግረሃል" ሲሉ መረጃው የመጣው ከመከላከያ ሚኒስትሩ ንግግር እንደሆነ ገልጸዋል። ባለፈው ወር የነበረውን የሴኔት ስብሰባ የሚያሳይ ቪዲዮም ለጥፈዋል።

    "ይህ ምሥጢራዊ መረጃ አይደለም፤ የአንተ ንግግር ነው። ይህ ጦርነት ከፍተኛ ዋጋ እያስወጣ ነው፤ አንተ እና ፕሬዝዳንቱ እስካሁን ድረስ [የጦርነቱ] ግብ ምን እንደሆነ ለአሜሪካ ሕዝብ አላብራራችሁም" ሲሉ ወቅሰዋል።

    የመከላከያ ሚኒስትሩ ሄግሴት ሴናተር ኬሊ ላይ ምርመራ እንዲደረግ የጠየቁት ከዚህ ቀደም ባደረጉት ንግግር ምክንያት የተነሳው ውዝግብ ባልተቋጨበት ወቅት ነው። ሴናተሩ ከዚህ ቀደም የአሜሪካ ወታደሮች ሕገ-ወጥ ትዕዛዞችን እንዳይቀበሉ ሲናገሩ ተደምጠው ነበር።

    መከላከያ መሥሪያ ቤቱ በዚህ ንግግራቸው ምክንያት ሕጋዊ እርምጃ ሊወስድባቸው ያቀደ ሲሆን፣ ከቀናት በፊት ግን የፌዴራል ይግባኝ ሰበር ችሎት የፔንታገንን እርምጃ ውድቅ ሊያደርግ እንደሚችል ተሰምቷል።

  7. የቴህራን ጎዳናዎችን የሞሉት የኢራን መንግሥት የፕሮፓጋንዳ ሥዕሎች

    ግድግዳ ላይ በተሳለ ስዕል አጠገብ የምታልፍ ሴት

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የካቲት ላይ የተጀመረው የኢራን ጦርነት መቋጫ ሳያገኝ ወደ ሦስተኛ ወር እያመራ ነው። ሁለቱ አገራት ስምምነት የመፈጸማቸው ጉዳይ እስካሁን ተጨባጭ የሚባል ሁኔታ ላይ አልደረሰም።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢራን መንግሥት ዋና ከተማዋ ቴህራን ውስጥ የሚያስቀምጣቸው የፕሮፖጋንዳ ቢልቦርዶች እና የግድግዳ ሥዕሎች እየጨመሩ መጥተዋል።

    የከተማዋ ነዋሪዎች በአንጻሩ የሚፈጸመው ጥቃት እንዲገታ ባደረገው ተኩስ አቁም ጥላ ስር ሆነው የዘውትር ሕይወታቸውን ቀጥለዋል።

    የቴህራን ነዋሪዎች እንቅስቃሴ እና የጎዳና ላይ ሥዕሎቹን የሚያሳዩትን ምሥሎች ይመልከቱ

    ግድግዳ ላይ በተሳለ ስዕል አጠገብ የሚያልፉ ወጣቶች

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    ግድግዳ ላይ በተሳለ ስዕል አጠገብ የምታልፍ ሴት

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    በቢልቦርድ አጠገብ የምታልፍ ሴት

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    ግድግዳ ላይ በተሳለ ስዕል አጠገብ የምታልፍ ሴት

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

  8. ኢራን ለአሜሪካ የስምምነት ዕቅድ የሰጠሁት ምላሽ “ምክንያታዊ እና ለጋስ” ነው አለች

    ኢራን ጠቅላይ መሪ በተሳሉበት ግድግዳ በኩል የምታልፍ ሴት

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ቴህራን በአሜሪካ ለቀረበው የድርድር ዕቅድ የሰጠችው ምላሽ “ምክንያታዊ እና ለጋስ” እንደሆነ በመግለጽ፤ አሜሪካን ግን “ለአንድ ወገን ያደላ እና ምክንያታዊ ያልሆነ” አቋም ላይ ጸንታለች የሚል ክስ አቀረቡ።

    ኢራን ባለፈው ሳምንት በአሜሪካ ለቀረበው የድርድር ዕቅድ በአሸማጋይዋ ፓኪስታን በኩል ምላሽ መስጠቷን ያሳወቀችው ትናንት እሁድ ነበር። የቴህራን ምላሽ ያላስደሰታቸው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለው” በማለት ውድቅ አድርገውታል።

    የኢራን ዜና ወኪል ዘገባ እንደሚያሳየው ቴህራን የሰጠችው ምላሽ በሁሉም ግንባሮች የሚካሄዱ ውጊያዎች እንዲቆሙ እና አሜሪካ በኢራን ወደቦች ላይ የጣለችው እገዳ እንዲነሳ ይጠይቃል። ወደፊት ኢራን ላይ ጥቃት እንደማይፈጸም ዋስትና የመስጠት ጉዳይም ምላሹ ውስጥ ተካትቷል።

    ዛሬ ሰኞ ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡት የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ኢስማኢል ባጋኢ፤ ቴህራን "ከሕጋዊ መብቶቿ" ውጭ የሆነ ጥያቄ እንዳላቀረበች ተናግረዋል።

    እንደ ቃል አቀባዩ ገለጻ የኢራን ምላሽ “በቀጣናው የሚደረገው ጦርነት እንዲያበቃ”፣ “የባሕር ላይ እገዳ ተብሎ የሚገለጸው በኢራን መርከቦች ላይ የሚፈጸመም የባሕር ላይ ውንብድና እንዲቆም” እንዲሁም “በውጭ ባንኮች የታገደውና የኢራን ሕዝብ ንብረት የሆነው ሀብት እንዲለቀቅ” የሚጠይቅ ነው።

    ቃል አቀባዩ “እንዲሁም በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል አስተማማኝ የባሕር ጉዞ እንዲኖር ያቀረብነው ሐሳብ ከመጠን ያለፈ ጥያቄ ነውን? ሊባኖስን ጨምሮ በመላው ቀጣናው ሰላም እንዲሰፍን መጠየቅስ እንዴት ከልክ ያለፈ ጥያቄ ሆኖ ሊታይ ይችላል?” በማለት ጠይቀዋል።

    በዕቅዱ ውስጥ የተካተቱት ነጥቦች "ምክንያታዊ እና ለጋስ" መሆናቸውን የተናገሩት ባጋኢ፤ በአንጻሩ ግን አሜሪካ "ምክንያታዊ ያልሆኑ ጥያቄዎችን" እያቀረበች ነው ሲሉ ከስሰዋል።

    ፓኪስታን ውስጥ በተደረገው የመጀመሪያው ዙር ድርድር ሁለቱን አገራት ያላስማማቸው ዋነኛ ጉዳይ የኢራን የኒውክሌር ፕሮግራም ነበር።

    ከዚህ ቀደም ኢራን የኒውክሌር ጉዳይ ለጊዜው ወደ ጎን ተደርጎ በቅድሚያ ጦርነቱን ማቆም እና ሆርሙዝን መክፈት የተመለከተ ንግግር እንዲደረግ የሚጠይቅ ዕቅድ አቅርባ የነበረ ቢሆንም፤ አሜሪካ አልተቀበለችውም።

  9. ሦስት ድፍድፍ ነዳጅ የጫኑ ግዙፍ መርከቦች መከታተያቸውን በማጥፋት የሆርሙዝ ወሽመጥን ማቋረጣቸውን ሮይተርስ ዘገበ

    በሆርሙዝ ወሽመት የሚንቀሳቀሱ መርከቦች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ባለፈው ሳምንት ሦስት ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ራሳቸውን ከኢራን ጥቃት ለመከላከል የመከታተያ መሣሪያቸውን በማጥፋት ወሽመጡን ማቋረጣቸውን ሮይተርስ ዘገበ።

    ሮይተርስ የመርከቦች እንቅስቃሴን ከሚከታተሉት ኬፕለር እና ኤልኤስኢጂ ያገኘውን መረጃ ጠቅሶ እንደዘገበው ሁለት ግዙፍ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ሆርሙዝን ያቋረጡት ትናንት እሁድ ነው።

    አንዱ መርከብ ግን ከአምስት ቀን በፊት ማቋረጡን የመርከቦችን እንቅስቃሴ የሚከታተሉትን ድርጅቶች ጠቅሶ ዘግቧል።

    አጊዮስ ፋኖውሪየስ I እና ኪያራ ኤም የተሰኙት መርከቦች እያንዳንዳቸው ሁለት ሚሊየን በርሜል ነዳጅ መጫናቸው ተግለጿል።

    አጊዮስ ፋኖውሪየስ I ወደ ቬይትናም የሚያመራ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን ከዚህ ቀደም ሁለቴ ወሽመጡን ለማቋረጥ ያደረገው ሙከራ ሳይሳካ ቀርቷል።

    አጊዮስ ፋኖውሪየስ I የሚያስተዳድረው ኢስተርን ሜዲትራኒያን ማሪታይም ስለመርከቡ ጉዞ አስተያየት ከመስጠት ተቆጥቧል።

    እሁድ ዕለት ወሽመጡን ያቋረጠው ሌላው ነዳጅ ጫኝ መርክ ኪያራ ኤም የጫነውን ነዳጅ ወዴት እንደሚያጓጉዝ አልታወቀም። መርከቡን የሚያስተዳድረው መቀመጫውን ሻንጋይ ያደረገው ኩባንያ ሲሆን ስለ መርከቡም ሆነ ስለ ጭነቱ የቀረበለትን ጥያቄ ሳይመልስ መቅረቱን ሮይተርስ ዘግቧል።

    ቀደም ብሎ ከአቡዳቢ ብሔራዊ የነዳጅ ኩባንያ 2 ሚሊዮን በርሜል ነዳጅ የጫነ መርከብ እአአ ግንቦት 6 የመከታተያ መሣሪያውን በማጥፋት አቋርጧል።

    አሜሪካ እና ኢራን ከሁለት ወር በፊት የገቡበት ጦርነትን ተከትሎ የሆርሙዝ ወሽመጥ በመዘጋቱ የነዳጅ፣ ጋዝ፣ ፔትሮል፣ ፕላስቲክ እና የምግብ ዋጋ ንሯል።

  10. ከኢራን ጦርነት በቢሊዮን ዶላር ትርፍ ያገኙት እነማን ናቸው?

    በፋብሪካ አካባቢ የቆመ ሰው

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የካቲት መጨረሻ የተጀመረው የኢራን ጦርነት በመላው ዓለም ተጽዕኖው ተሰምቷል። በአንጻሩ ጦርነቱ በረከት የሆነላቸው ኩባንያዎች እና ዘርፎችም አሉ። የነዳጅ አከፋፋይ ኩባንያዎች በዚህ ጦርነት ትርፍ ካጋበሱት መካከል ናቸው።

    ከዓለም የነዳጅ እና የጋዝ ጭነት አንድ አምስተኛ ያህሉ የሚጓጓዝበት የሆርሙዝ ወሽመጥ፤ ከየካቲት መጨረሻ ጀምሮ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ተዘግቷል።

    ይህንን ተከትሎ የአውሮፓ የነዳጅ ኩባንያዎች ከፍተኛ ትርፍ አጋብሰዋል። በወሽመጡ መዘጋት ምክንያት የዋጋ ጭማሪ በማድረግ ከፍተኛ የሚባል ትርፍ አግኝተዋል።

    'ቢፒ' የተባለው የብሪታኒያ የነዳጅ ኩባንያ በ2026 የመጀመሪያዎቹ ሦስት ወራት ትርፉ ከእጥፍ በላይ አድጎ 3.2 ቢሊዮን ዶላር ደርሷል።

    ሌላኛው የነዳጅ ኩባንያ 'ሼል' ደግሞ በመጀመሪያው ሩብ ዓመት 6.92 ቢሊዮን ዶላር በማግኘት ተንታኞች ከጠበቁት በላይ ትርፍ አስመዝግቧል።

    ግዙፉ ዓለም አቀፍ ኩባንያ 'ቶታል ኤነርጂስ’፣ በነዳጅ እና በኢነርጂ ገበያ ዋጋ መናር ምክንያት ትርፉ በአንድ ሦስተኛ ገደማ ጨምሯል። በሦስት ወራት ውስጥ ያገኘው ትርፍም 5.4 ቢሊዮን ዶላር እንደሆነ አስታውቋል።

    በአንጻሩ የአሜሪካዎቹ ኩባንያዎች 'ኤክሶንሞቢል' እና 'ቼቭሮን' በመካከለኛው ምሥራቅ የነዳጅ አቅርቦት መስተጓጎል ምክንያት ገቢያቸው ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ጊዜ ጋር ሲነጻጸር ዝቅ ብሎ ቢታይም፤ ያገኙት ትርፍ ከባለሙያዎች ግምት የበለጠ ነው።

    የነዳጅ ዋጋ ጦርነቱ ከመጀመሩ በፊት ከነበረው በእጅጉ የጨመረ በመሆኑ፤ የሁለቱም ኩባንያዎች ትርፍ እያደገ እንደሚሄድ ይጠበቃል።

  11. ኔታንያሁ እስራኤልን ከአሜሪካ ድጋፍ ማላቀቅ እንደሚፈልጉ ለሲቢኤስ ተናገሩ

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ አገራቸውን ከአሜሪካ ወታደራዊ ድጋፍ ለማላቀቅ እንደሚፈልጉ ተናገሩ።

    ኔታንያሁ እሁድ ዕለት ከሲቢኤስ ጋር በነበራቸው ቃለ ምልልስ ወቅት በሚቀጥሉት አስርት ዓመታት ከባሕረ ሰላጤው አገራት ጋር ያላቸውን ግንኙነት በማጠናከር ከአሜሪካ የሚያገኙትን ወታደራዊ ድጋፍ ለመቀነስ ጥረት እንደሚያደርጉ ተናግረዋል።

    ኔታንያሁ ለሲቢኤስ ኒውስ "60 ደቂቃ" ፕሮግራም እንደተናገሩት "የአሜሪካን የገንዘብ ድጋፍ፣ ባለን ወታደራዊ ትብብር ላይ ያለው የገንዘብ ድጋፍን፣ ወደ ዜሮ ማውረድ እፈልጋለሁ” ብለዋል።

    ኔታንያሁ እንዳሉት እስራኤል በዓመት 3.8 ቢሊዮን ዶላር የአሜሪካን ወታደራዊ እርዳታ ታገኛለች። ዩናይትድ ስቴትስ እአአ ከ2018 እስከ 2028 በድምሩ 38 ቢሊዮን ዶላር ወታደራዊ ድጋፍ ለእስራኤል ለመስጠትተስማምታለች።

    የዩናይትድ ስቴትስ እና የእስራኤል የገንዘብ ድጋፍ ትብብር ለመለወጥ “ፍጹም” ትክክለኛው ጊዜ ነው ሲሉ ኔታንያሁ ተናግረዋል። ቀጣዩ ምክር ቤት እስኪመጣ ድረስ "መቆየት አልፈልግም” ያሉት ኔታንያሁ፣ “አሁን መጀመር እፈልጋለሁ” ብለዋል።

    እስራኤል ለረዥም ዓመታት በሁለቱም ፓርቲዎች የሥልጣን ዘመን ጠንካራ ወታደራዊ ድጋፍ ስታገኝ ቆይታለች። ነገር ግን በ2016 ዓ.ም. የጋዛ ጦርነት መቀስቀሱን ተከትሎ ከአሜሪካ ሕግ አውጪዎች እና ሕዝብ የሚገኘው ድጋፍ እየቀነሰ መትቷል።

    በመጋቢት ወር የተሰበሰበ የሕዝብ አስተያየት እንደሚያሳየው 60 በመቶ አሜሪካውያን ለእስራኤል አሉታዊ አስተያየት ያላቸው ሲሆን፤ 59 በመቶ ዎቹ በቤንያሚን ኔታንያሁ ላይ ያላቸው እምነት ዝቅተኛ መሆኑን ተናግረዋል።

  12. ቻይና ቴህራን ላይ የሚጣል ማዕቀብ ኩባንያዎቼን ይጎዳል በሚል ተቃወመች

    የቻይና እና የአሜሪካ ባንዲራዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አሜሪካ መቀመጫቸውን ቻይና ባደረጉ ሦስት ኩባንያዎች ላይ የጣለችውን ማዕቀብ ቤይጂንግ ተቃወመች።

    ቤይጂንግ ተቃውሞዋን ያሰማችው ኩባንያዎቹ የኢራንን ወታደራዊ እንቅስቃሴ ደግፈዋል በሚል ውንጀላ ከቀረበባቸው በኋላ ነው።

    ሰኞ ዕለት ጠንካራ ተቃውሞዋን የገለጸችው ቤይጂንግ ማዕቀቦቹን ሕገ ወጥ እና የአንድ ወገን ውሳኔ ብላ ጠርታዋለች።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ የሆኑት ጉኦ ጂያኩን “ምንጊዜም የቻይና ኩባንያዎችን ሥራቸውን በሕግ እና መመሪያዎች መሠረት እንዲያከናውኑ እናደርጋለን፤ እንዲሁም የቻይና ኢንተርፕራይዞችን ሕጋዊ መብቶች እና ጥቅሞች በጽኑ እንጠብቃለን” ሲሉ ተናግረዋል።

    "ሌሎች አገራትን በስህተት ከመኮነን እና ከመተቸት አንገብጋቢው እና ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ ጦርነቱ ዳግም እንዳይጀመር መከላከል ነው” ብለዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከዢ ጂንፒንግ ጋር ለመገናኘት በዚህ ሳምንት ወደ ቻይና ያመራሉ። ከግንቦት 5 እስከ 7 2018 ዓ.ም. የሚቆየው ይህ ጉብኝት በአስር ዓመታት ውስጥ አንድ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ወደ ቻይና የሚያደርጉት የመጀመሪያው ጉዞ ይሆናል ተብሏል፡፡

  13. ትራምፕ የኢራንን የሰላም ዕቅድ ውድቅ ካደረጉ በኋላ የነዳጅ ዋጋ ጨመረ

    ናፍጣ የሚቀዳ ሞተር ሳይክል

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ለአሜሪካ የሰላም ዕቅድ የሰጠችውን ምላሽ ውድቅ ካደረጉ በኋላ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ አሳየ።

    ቴህራን ምላሹን የሰጠችው በአደራዳሪዋ ፓኪስታን በኩል ሲሆን ግጭቱ ወዲያውኑ እንዲቆም እንዲሁም ከዚህ በኋላ ምንም ዓይነት ጥቃት እንደማይፈጸምባት ማረጋገጫ እንዲሰጣት መጠየቋን ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ሰኞ ዕለት ብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ በእስያ ገበያ በበርሜል የ4.1 በመቶ ጭማሪ በማሳየት 105.50 ዶላር ተሸጧል።

    የዓለም 20 በመቶ ነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ መተላለፊያ የሆነው ሆርሙዝ ከየካቲት የመጨረሻ ሳምንት ጀምሮ በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ጦርነት በመቀስቀሱ ዝግ ሀኗል።

    ጦርነቱ ከጀመረ ጊዜ አንስቶ የዓለም የነዳጅ ዋጋ በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ የመጣ ሲሆን የብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ በበርሜል ከ100 ዶላር በላይ እየተሸጠ ይገኛል።

    የዓለም አንድ አምስተኛው ነዳጅ የሚተላለፍበት የሆርሙዝ ወሽመጥ ከተዘጋ በኋላ ቴህራን ለማቋረጥ የሚሞክሩ መርከቦች ላይ ጥቃት እንደምትፈጽም በመግለጽ አስጠንቅቃለች።

    ጦርነቱ ከተጀመረበት የካቲት 21/ 2018 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ ግንቦት ድረስ የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማቋረጥ የሞከሩ 26 የነዳጅ እና ኮንቴይነር ጫኝ መርከቦች ላይ ጥቃት መፈጸሙ ተገልጿል።

    መርከቦቹ ላይ ጥቃት የደረሰው በተወንጫፊዎች፣ በአነስተኛ ጀልባዎች፣ በቦምብ ሲሆን አብዛኞቹ ጥቃቶች የተፈጸሙት ከኦማን የባሕር ዳርቻ ወጣ ባለ ስፍራ እንዲሁም የዩኤኢ ፉጃይራህ ወደብ አቅራቢያ ነው።

    ዓለም አቀፉ የባሕር ላይ ትራንስፖርት ድርጅት በሆርሙዝ ወሽመጥ ከ1500 እስከ 2000 መርከቦች እንዲሁም 20 ሺህ ባህረተኞች መንቀሳቀሻ አጥተው መቆማቸውን አስታውቋል።

    ዋና ዋና የኢነርጂ ኩባንያዎች የዓለም የነዳጅ እና የጋዝ ዋጋ ጭማሪ ማሳየቱን ተከትሎ ትርፋቸው መጨመሩን ይፋ አድርገዋል።

    እሁድ ዕለት አራምኮ ባለፉት ሦስት ወራት ያገኘው ትርፍ ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ጊዜ ጋር ሲነጻጸር የ25 በመቶ ጭማሪ ትርፍ ማግኘቱን አስታውቋል።

    ባለፈው ወር እንዲሁ ቢፒ የመጀመሪያዎቹ ሦስት ወራት ትርፉ ከእጥፍ በላይ መጨመሩን የገለጸ ሲሆን ሼል ደግሞ ባለፈው ሳምንት ትርፉ ከፍ ማለቱን ተናግሯል።

  14. ኢራን በወሽመጡ ላይ የሚሰማሩ የፈረንሳይ እና የብሪታኒያ ባሕር ኃይሎችን አስጠነቀቀች

    ቴህራን የዓለም አንድ አምስተኛ የነዳጅ ዘይት እና የተፈጥሮ ጋዝ የሚጓጓዝበትን መስመር አሜሪካ እና እስራኤል ጦርነት ከከፈቱባት የካቲት 21 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ሙሉ በሙሉ ዘግታዋለች።

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የፈረንሳይ ወይም የብሪታኒያ ባሕር ኃይሎች የሚሰማሩ ከሆነ “ወሳኝ እና ፈጣን ምላሽ” እንደምትሰጥ አስጠነቀቀች።

    የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ማክሮን አገራቸው በወሽመጡ ላይ የባሕር ኃይሏን ለማሰማራት “ዕቅድ እንደሌላት” ገልጸው ነገር ግን “ከኢራን ጋር በመተባበር” የደህንነት ተልዕኮ የሚሰጠው ጦር እንደሚሆን ተናግረዋል።

    ቅዳሜ ዕለት የብሪታኒያ ባሕር ኃይል በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የሚኖርን የመርከቦች እንቅስቃሴ ለመከላከል የሚደረግ ዓለም አቀፍ ተልዕኮ ላይ ለመሳተፍ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ የጦር መርከቡን መላኩን አስታውቋል።

    የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር እና የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት በጋራ በመሆን ጦርነቱ ካበቃ በኋላ ይጀመራል የተባለውን ይህንን ዓለም አቀፍ ተልዕኮ ደግፈው ተናግረዋል።

    ሰኞ ዕለት ከ40 አገራት በላይ የሚውጣጡ የመከላከያ ሚኒስትሮች በዩኬ የበላይነት የሚመራውን እና በወሽመጡ ላይ የሚደረግ የመርከብ እንቅስቃሴን የመከላከል ዘመቻ ዕቅድ ላይ ተገናኝተው ይወያያሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    የዩኬው ኮን ሄይሊ እና የፈረንሳዩ አቻቸው ካትሪን ቫውትሪን በጋራ በመሆን ስብሰባውን የሚመሩ ሲሆን ጦርነቱ ከቆመ በኋላ በወሽመጡ ላይ የሚደረጉ የመርከብ እንቅስቃሴዎችን እንዴት እንደሚጠብቁ ይመካከራሉ ተብሏል።

    ቴህራን የዓለም አንድ አምስተኛ የነዳጅ ዘይት እና የተፈጥሮ ጋዝ የሚጓጓዝበትን መስመር አሜሪካ እና እስራኤል ጦርነት ከከፈቱባት የካቲት 21/2018 ዓ.ም. ጀምሮ ሙሉ በሙሉ ዘግታዋለች።

    የኢራን ጦር ቃል አቀባይ ሞሐመድ አክራሚኒያ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚያልፉ መርከቦች ከቴህራን ጋር በቅድሚያ የማይተባበሩ ከሆነ “ከባድ እርምጃ” እንደሚወሰድባቸው ማስጠንቀቃቸውን የኢርና የዜና ወኪል ዘግቧል።

    አክራሚኒያ አክለውም አሜሪካኖች “ይህንን በሰሜን ሕንድ ውቅያኖስ የሚገኝ ሰፊ የባሕር ክፍል በጦር መርከቦቻቸው ቢሞሉት እንኳ ሙሉ በሙሉ መዝጋት አይችሉም" ሲሉ ተናግረዋል።

    አሜሪካ በባሕረ ሰላጤው አገራት በኳታር፣ ባህሬን፣ ኩዌት፣ ዩኤኢ፣ ሳዑዲ አረቢያ እና ኦማን የጦር ሠፈሮች አሏት።

  15. ትራምፕ ኢራን ለሰላም ዕቅዱ የሰጠችውን ምላሽ ውድቅ አደረጉ

    ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን አሜሪካ ጦርነቱን ለማቆም ላቀረበችው ዕቅድ የሰጠችውን ምላሽ “ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለው” ሲሉ ውድቅ አደረጉ።

    በከፊል ከኢራን መንግሥት ጋር ግንኙነት ያለው ታስኒም የቴህራን ምላሽ በአሸማጋይዋ ፓኪስታን በኩል መላኩን ዘግቧል።

    የዜና ወኪሉ የቴህራን ምላሽ ውስጥ በሁሉም ግንባሮች የሚካሄዱ ውግያዎች እንዲቆሙ፣ አሜሪካ የኢራን ወደቦች ላይ የጣለችው እገዳ እንዲነሳ፣ እንዲሁም ወደፊት ኢራን ላይ ጥቃት እንደማይፈጸም ዋስትና እንዲሰጥ ይጠይቃል።

    ከሁለት ወር በላይ በዘለቀው የኢራን ጦርነት አልፎ አልፎ የተኩስ ልውውጦች ቢኖሩም በአብዛኛው የተኩስ አቁሙ እንደቀጠለ ነው።

    ከዚህ ሳምንት ቀደም ብሎ ትራምፕ በኢራን ላይ የከፈቱት ጦርነት “በፍጥነት ይጠናቀቃል” ብለው ነበር።

    ነገር ግን የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ጦርነቱ ተጠናቅቋል ከማለታችን በፊት ኢራን ያከማቸችው የበለጸገ ዩራኒየም “መውጣት አለበት” ሲሉ ጠይቀዋል።

    ኔታንያሁ ሲቢኤስ ላይ በሚቀረበው ‘60 ሚኒትስ’ ለተሰኘ ፕሮግራም በሰጡት ቃለ ምልልስ “አሁንም ያልወደሙ የማበልጸጊያ ማዕከላት አሉ” ብለዋል።

    እሁድ ዕለት የኢራኑ ፕሬዚዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን የሰላም ዕቅዱን በቀጥታ ሳይጠቅሱ “በጠላቶቻችን ፊት አንገታችንን አንደፋም። የንግግር ወይም የድርድር ሃሳብ ሲመጣ እጅ መስጠት ወይም ማፈግፈግ ማለት አይደለም” ብለዋል።

    ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ “በተወካይ በኩል ቀረበ የተባለውን የኢራንን ምላሽ አነበብኩት፤ አልወደድኩትም። ምንም ተቀባይነት የለውም” ሲሉ ጽፈዋል።

    የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን የሆነው አክሲዮስ ውስጥ አዋቂ ምንጮችን ጠቅሶ እንደዘገበው አሜሪካ ያቀረበችው ባለ 14 ነጥብ የሰላም ዕቅድ ኢራን ኒውክሌር ማበልጸጓን እንድታቋረጥ፣ የተጣለባት ማዕቀብ እንዲነሳ እና በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የሚደረገው ነጻ እንቅስቃሴ እንዲቀጥል የሚጠይቁ ሃሳቦችን የያዘ ነው።

    መገናኛ ብዙኃኑ በዘገባው ስለ ዕቅዱ ማብራሪያ የተሰጣቸውን ሁለት በስም ያልተጠቀሱ የአሜሪካ ባለሥልጣናትን እና ሁለት ሌሎች ግለሰቦችን ጠቅሷል።

    እንዚህ ምንጮች በመግባቢያ ሰነዱ ላይ የተጠቀሱት አብዛኛዎቹ ነጥቦች ለመጨረሻው ስምምነት መነሻ በመሆን ያገለግላሉ ብለዋል።

    ኢራን የዓለም 20 በመቶ ነዳጅ እና ጋዝ የሚተላለፍበትን የባሕር ወሽመጡን እንደዘጋች ነው።

    አሜሪካ በበኩሏ ወደ ኢራን ወደቦች የሚገቡ እና የሚወጡ መርከቦችን የከለከለች ሲሆን ይህም ቴህራን ወደ ድርድር ጠረጴዛ እንድትመጣ ጫና ለመፍጠር ያለመ ነው።

    ትራምፕ እአአ ግንቦት 6 በትሩዝ ሶሻል ሚዲያ ገጻቸው ላይ ኢራን በቀረበላት የሰላም ሃሳብ የማትስማማ ከሆነ ዳግመኛ የቦምብ ድብደባው እንደሚጀመር ጽፈው “ከዚህ በፊት ከታየው ሁሉ የከፋ ይሆናል” ሲሉ አስጠንቅቀው ነበር።