ቅርስ፡ በአየር ንብረት ለውጥ አደጋ የተጋረጠባቸው ስድስቱ የአፍሪካ ቅርሶች

የፎቶው ባለመብት, GETTY
በደቡባዊና ምስራቃዊ አፍሪካ ከሚገኙት የአለት ላይ ጥበቦች እስከ የአባይ ወንዝን ተከትሎ የተሰሩት ፒራሚዶች ድረስ አፍሪካውያን የጥበብ አሻራቸውን ላለፉት በሺዎች ለሚቆጠሩ ዓመታት ሲያሳርፉ ቆይተዋል።
ነገር ግን አስከፊ የአየር ጸባይ፣ የባህር ጠለል ከፍታ መጨመረ እንዲሁም ሌሎች ከአየር ጸባይ ለውጥ ጋር የተያያዙ ጋሬጣዎች በአፍሪካ ታሪክ እጅግ ውድ የሆኑትን ቅርሶች አደጋ ላይ እየጣሏቸው መሆኑን በቅርቡ የተሰራ አንድ ጥናት ጠቁሟል።
'አዜኒያ' ለተባለው ጆርናል ሀሳባቸውን ካካፈሉ የኬንያ፣ የዑኬና አሜሪካ ተመራማሪዎች 'ፈጣንና ውጤታማ እርምጃ' ካለተወሰደ እነዚህን ቅረሶች ማዳን አይቻልም ብለዋል።
በቅርብ ሳምንት ደግሞ በሱዳን የሚገኙ አርኪዮሎጂስቶች በተባበሩት መንግስታት የተመዘገበው አል ባጅራዊያና በአገሪቱ ካጋጠመው የጎርፍ መጥለቅለቅ አደጋ ለማዳን ሲንቀሳቀሱ ነበር።
ጎርፉ የተከሰተው የአባይ ወንዝ በመሙላቱ ሲሆን ይህን ክስተት በየዓመቱ መመልከት የተለመደ ነገር ከሆነ ሰነባብቷል። ነገር ግን ውሃው እንደ ዘንድሮው በከፍተኛ ሁኔታ ተሰራጭቶ አይተው እንደማያውቁ ነዋሪዎች ገልጸዋል።
'አዜኒያ ጆርናል' ላይ ሀሳባቸውን ያሰፈሩት ባሉያዎች ደግሞ በመላው አፍሪካ አደጋ የተጋረጠባቸው ያሏቸውን ስድስት ቅርሶች ዘርዝረዋል።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ሱአኪን፡ ሱዳን
በሰሜን ምስረቃዊ ሱዳን የምትገኘው ሱአኪን በአንድ ወቅት በቀይ ባህር ላይ የምትገኝ እጅግ በጣም ወሳኝ የወደብ ከተማ ነበረች።
የሱአኪን ታሪክም የጀመረው ከ3 ሺ ዓመታት በፊት ሲሆን የግብጽ ፈረኦኖች ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታዋ ከፍተኛ የነበረችውን ከተማ ወደ የንግድና አሰሳ ማዕከልነት ቀይረዋታል።
በዛውም ሱአኪን የእስልምና እምነት ተከታዮች ወደ መካ በሚያደርጉት ጉዞ ላይ ቁልፍ ሚና መጫወት ጀመረች። በተጨማሪም በቀይ ባህር ላይ ይከናወኑ የነበሩ የባሪያ ንግዶችም በዝችው ወደብ በኩል ነበር የሚሳለጡት።
ይሄው የወደብ ከተማ በኦቶተማን ኢምኦኣየር ስር ወድቆም ነበር።
ምንም እንኳን በአሁኑ ሰአት የዝህች የወደብ ከተማ ቅሪቶች ብቻ ቢሆኑም የሚገኙት በአካባቢው የሚገኙት የቀድሞ መኖሪያ ቤቶች እና መስጂዶች በተባበሩት መንግስታት የባህል ድርጅት ዩኔስኮ በአፍሪካ ቅርስነት ተመዝግበዋል።
አሁን ላይ የሚገኙት በርካታ ቅሪቶችም በስብሰውና የቀድሞ ግርማ ሞገሳቸውን አጥተው ይታያሉ።
ለዚህ ደግሞ ዋነኛ ምክንያቱ የቀይ ባህር ጠለል መጨመርና መቀነስ፣ የባህር ዳርቻ መሸርሸርና ሌሎች ከአየር ንብረት ጋር የተያያዙ ጉዳዮች ናቸው። አሁን እየሆነ ያለው ነገር በዚሁ የሚቀጥል ከሆነ ደግሞ ይህ ቅርስ በቅርብ ዓመታት ውስጥ ሊጠፋ እንደሚችል ባለሙያዎቹ ገልጸዋል።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ላሙ የድሮ ከተማ፡ ኬንያ
በዩኔስኮ መረጃ መሰረት የላሙ የድሮ ከተማ በምስራቅ አፍሪካ በአግባቡ ተጠብቀው ከሚገኙ የስዋሂሊ ሰፈሮች መካከል በእድሜ ትልቁ ነው።
ከሌሎቹ የምስራቅ አፍሪካ የባህር ዳርቻ ከተሞችና መንደሮች በተለየ መልኩ ላሙ ላለፉት 700 ዓመታት ሰዎች ሲኖሩበት ነበር። ሌሎቹ ሰፈራዎች ግን ለበርካታ ዓመታት ሰዎች ሳይኖሩባቸው ቆይተዋል።
የላሙ ከተማ የስዋሂሊ እና የእስልምና ባህልን ለማጥናት ማዕከልም ነው።
ነገር ግን ላሙ በአሁኑ ሰአት የባህር ዳርቻ ውሃ በመሸሹ ምክንያት ክፉኛ እየተጎዳ ነው። ይህ ማለት ደግሞ አሸዋውና በባህር ላይ የሚገኙ ተክሎች ያቀርቡት የነበረውን ተፈጥሮአዊ መከላከል ያሳጣዋል።
ከዚህ በተጨማሪ ደግሞ በድሮው ላሙ የተገነባው ትልቅ የወደብ ከተማ በአካባቢው ያለውን ተፈጥሮአዊ ጫካ ከመጉዳቱ ባለፈ ከተማውን ለከፍተኛ የጎርፍ አደጋ አጋልጦታል።
ባለሙያዎቹም ተፈጥሮአዊውን ሀብት በጎዳነው ቁጥር ሰው ሰራሽ የሆኑትን ባህሎቻችንንም ጭምር ነው እየጎዳን ያለነው ብለዋል።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የኮሞሮስ ባህር ዳርቻ አካባቢዎች
በኮሞሮስ የሚገኙትና በእሳተ ገሞራ አማካይነት የተፈጠረው የደሴቶች ስብስብ እንደ ቤተመንግስት የመሳሰሉ በደንብ ተጠብቀው የሚገኙ ቅርሶችን ይዟል። እነዚህ ቅርሶች በመቶዎች ለሚቆጠሩ ዓመታት በዚህ ስፍራ እንደቆዩ ይታመናል።
ነገር ግን ከባህር ጠለል ከፍ ማለት ጋር ተያይዞ ይህ ቅርስ አደጋ ተጋርጦበታልእእ።
በዓለማችን ላይ እየጨመረ የመጣው የካርቦን ልቀት በበርካታ የአፍሪካ ባህር ዳርቻዎች አካባቢ ላይ ቀላል የማይባል ተጽህኖ እያሳደረ መሆኑን ባለሙያዎቹ አሳስበዋል።
እአአ በ2050 ደግሞ እንደ ጊኒ፣ ጋምቢያ፣ ናይጄሪያ፣ ቶጎ፣ ቤኒን፣ ኮንጎ፣ ቱኒዚያ፣ ታንዛኒያ እና ኮሞሮስ ያሉ አገራት በባህር ዳርቻዎቻቸው አካባቢ ከፍተኛ መሸርሸር እና ውሀ መሸሽ እንደሚያጋጥማቸው ተንብየዋል።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የጋና የባህር ዳርቻ ቤተ-መንግስቶችና መናገሻዎች
የጋና የባህር ዳርቻ በ1482 እና 1786 ባሉት ዓመታት መካከል የተቋቋሙ የንግድ አካባቢዎች የሚገኘኑበት ሲሆን እስከ 500 ኪሎሜትር ድረስ እርዝማኔ እንዳለቸው ይነገራል።
ቤተመንግስቶቹ እና መናገሻዎቹ የተገነቡትና ይጠቀሟቸው የነበሩት በፖርቹጋል፣ ስፔን፣ ዴንማርክ፣ ስዊድን፣ ሆላንድ፣ ጀርምን እና ዩኬ ነጋዴዎች እንደሆኑም ይታወቃል።
የእነዚህ ቤተመንግስቶችና መናገሻዎች መገንባት ለአካባቢው የንግድ ቀጠና መሆን ትልቅ ሚና ተጫውተዋል።
ነገር ግን እነዚህ ቅርሶች ለባህር ጠለል መጨመርና ለአውሎ ነፋስ መጋለጣቸው ስጋት ውስጥ እንዲገቡ አድርጓቸዋል። በርካታ ቤተመንግስቶችም በባህር ውሀ እየተሸረሸሩና የድሮ ሞገስና ጥንካሬያቸውን እያጡ መሆኑ ተጠቁሟል።
ከዛሬ 50 ዓመት በፊት ከተነሱ ፎቶዎች ጋር በማነጻጸርም ምን ያክል ጉዳት እንደደረሰባቸው ማየት ይቻላል ብለዋል ተመራማሪዎቹ።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የትዌይፍልፎንቴይን የአለት ላይ ጥበብ፡ ናሚቢያ
የአየር ጸባይ ለውጥና በአካባቢው ያለው ደረቅ የአየር ጸባይ በእነዚህ የድንጋይ ላይ ቅርሶች ላይ ከፍተኛ ተጽህኖ እያሳረፉ ይገኛሉ። እነዚህ የድንጋይ ላይ ጥበቦች በአፍሪካ በከፍተኛ ቁጥር የሚገኙት ናሚቢያ ውስጥ ነው።
ዩኔስኮ እንደሚለው ቅርሱ '' ከፍተኛ የሆነ ጥራት ያለው ስዕል'' ሲሆን በደቡባዊ አፍሪካ በወቅቱ ይከናነወኑ የነበነሩ ስነስርአቶችን እንዲሁም የአደንና ምግብ ለቀማ ሂደቶችን ቁልጭ አልድሮ ማሳየት የሚችሉ ናቸው።
ባለፉት 2 ሺ ዓመታት የተከናወኑ ነገሮችንም መናገር የሚችልናቸ ትልቅ ትርጉም ያለው ቦታ ነው ይላል ዩኔስኮ። ነገር ግን በቅርብ ዓመታት ውስጥ ልናጣው እንችላለን።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ጄኔ፡ ማሊ
እስከ 2 ሺ ዓመታት ድረስ እድሜ እንዳስቆጠሩ የሚነገርላቸው እነዚህ የጭቃ ቤቶች ማሊ በዓለም ከምትታወቅባቸው ነገሮች መካከል የመጀመሪያዎቹ ናቸው። መንደሮቹ ከክርስቶስ ልደት በፊት በ250 ቢሲ በገበያ ማዕከልነት ሲያገከግሉ ነበር።
በ15ኛው እና 16ኛው ክፍለ ዘመን ደግሞ በምዕራብ አፍሪካ የእስልምና ትምህርት በስፋት የሚሰጥባቸው አካባቢዎች ነገሩ።
ነገር ግን የአየር ጸባይ ለውጥ የጭቃ ቤቶቹ የሚሰሩበትን ጭቃ በእጅጉ እየጎዳውና ተመሳሳይ ቤቶችን እንኳን መስራት እንዳይቻል አድርጓል።
የአካባቢው ነዋሪዎች እንደሚሉት ጭቃው እንደ ድሮው ጠንካራና ለዘዥም ዓመታት መቆየት የማይችል ሲሆን ያሉትን ለማደስና ወደ ቀድሞ ውበታቸው ለመመለስ አላስቻላቸውም።

















