አሜሪካ ሁዋዌ ኩባንያን እና የፋይናንስ ኃላፊዋን በማጭበርበር ከሰሰች

የፎቶው ባለመብት, Reuters
የአሜሪካ የፍትህ መስሪያ ቤት በቻይናው የቴሌኮም ግዙፍ ኩባንያ ሁዋዌ እና የኩባንያው የፋይናንስ ኃላፊ ሜንግ ዋንዡ ላይ ክስ መሰረተ።
በዓለማችን ቁጥር ሁለት የተንቀሳቃሽ ስልክ አምራች ኩባንያ ላይ ከተመሰረቱት ክሶች መካከል የባንክ ማጭበርበር፣ ፍትህን ማደናቀፍ እና የቴክኖሎጂ ስርቆት የሚሉ ይገኙበታል።
አሜሪካ በሁዋዌ ላይ የመሰረተችው ክስ ከቻይና ጋር የገጠመችውን የንግድ ጦርነት ወደለየት ደረጃ ከፍ ያደርገዋል፤ ሁዋዌም በመላው ዓለም ምርት እና አገልግሎቱን ለማስፋፋት የሚያደርገውን ጥረት ይገታዋል ተብሏል።
ኩባንያውም ሆነ የፋይናንስ ኃላፊዋ ሜንግ ክሶቹን ያጣጥላሉ።
የኩባንያው ባለቤት ልጅ እና የፋይናንስ ኃላፊ የሆኑት ሜንግ ዋንዡ በአሜሪካ ጥያቄ መሰረት ባሳለፍነው ወር ካናዳ ቫንኩቨር ከተማ ውስጥ በቁጥጥር ሥር እንዲውሉ መደረጉ ይታወሳል።
በወቅቱ በቁጥጥር ሥር እንዲውሉ ሲደረግ የቀረበው ምክንያት አሜሪካ በኢራን ላይ የጣለችውን ማዕቀብ ኩባንያው ተላልፏል የሚል ነበር።
''ለዓመታት የቻይና ኩባንያዎች ምርቶችን ወደ ውጪ በሚልኩበት ወቅት የአሜሪካ ሕጎችን ይጥሳሉ፤ ለማዕቀቦች ደንታ ቢስ ናቸው። ይህን ሁሉ ሕገ-ወጥ ተግባራት የሚፈጽሙት የአሜሪካንን የፋይናንስ ሥርዓት በመጠቀም ነው። ይህ መቆም አለበት'' ሲሉ የአሜሪካ የንግድ ቢሮ ኃላፊው ዊልበረ ሮስ ተናግረዋል።
ሁዋዌ የባንክ ማጭበርበር፣ ፍትህን ማደናቀፍ ከሚሉ ክሶች በተጨማሪ ቲ-ሞባይል ከተሰኘ የሞባይል ኩባንያ የሞባይ ስልኮች ዕድሜ ማራዘም የሚቻልበትን ቴክኖሎጂ ሰርቋል የሚል ከስ ተመስርቶበታል።
በጠቅላላው ሁዋዌ በአሜሪካ መንግሥት 23 ክሶች ተመስርቶበታል።
የአሜሪካው ኤፍቢአይ ዳይሬክተር ክርስቶፌር ዋሪይ ሁዋዌ የሃገራችንን እና የዓለምን የንግድ ሥርዓት ጥሷል ያሉ ሲሆን፤ ጨምረውም ''ሁዋዌ ለአሜሪካ ምጣኔ ሃብት እና ብሔራዊ ደህንነት አደጋ ደቅኗል'' ሲሉ ተደምጠዋል።
ሁዋዌ ከሳምሰንግ በመቀጠል በዓለማችን የቴሌኮሚኒኬሽን መሳሪያዎች አማራች እና አገልግሎት ሰጪ የሆነ ግዙፍ ኩባንያ ነው።

የፎቶው ባለመብት, Reuters
አሜሪካንን ጨምሮ ሌሎች ምዕራባውያን ሃገራት የቻይና መንግሥት ሁዋዌን ተጠቅሞ የስለላ አቅሙን ያሳድጋል ብለው ይሰጋሉ። ሁዋዌ ግን ከቻይና መንግሥት ጋር ምንም አይነት ግነኙነት የለኝም ይላል።
የሁዋዌ ኩባንያ ባለቤት ልጅ እና የፋይንስ ኃላፊዋ እስር ግን የቻይና መንግሥትን እጅጉን አስቆጥቷል።
ከሳምንታት በፊት በአሜሪካ ጥያቄ በካናዳ በቁጥጥር ሥር የዋሉት የፋይናንስ ኃላፊዋ ለጥቂት ቀናት በእስር ካሳለፉ በኋላ የ10 ሚሊዮን የካናዳ ዶላር ዋስ በመጥረት ከእስር ተለቀዋል።
ይሁን እንጂ የፋይናንስ ኃላፊዋ ለ24 ሰዓታት በክትትል ስር የሚገኙ ሲሆን ሙሉ እንቅስቃሴያቸውን የሚጠቁም ቁርጪምጪት ላይ የሚታሰር ኤሌክትሮኒክ መሳሪያ ማሰር ግድ ሆኖባቸዋል።














