የካናዳው ጠቅላይ ሚንስትር፡ ከሁዋዌ ባልደረባ እስር ጀርባ ፖለቲካ የለም

የሁዋዌ ባለቤት ልጅ

የፎቶው ባለመብት, Reuters

የካናዳ ጠቅላይ ሚንስትር ጀስቲን ትሩዶ ከሁዋዌ ባልደረባ እስር ጋር በተያያዘ የመንግሥታቸው እጅ እንደሌለበት አሳታወቁ።

የቻይናው ቴሌኮም ኩባንያ ሁዋዌ ባለቤት ልጅ እና ምክትል ኃላፊ ሜንግ ዋንዦ ካናዳ ቫንኮቨር አየር ማረፊያ ውስጥ ለእሥር መዳረጓ ይታወሳል።

ቻይና ሜንግ ዋንዦ በፍጥነት ከእስር እንድትለቀቅ የጠየቀች ሲሆን እስሩም የሰብዓዊ መብት ጥሰት ነው ብላለች።

የሥራ ኃላፊዋ ተጠርጥረው የታሰሩበት ጉዳይ ምን እንደሆነ ለህዝብ ይፋ አልተደረገም። ሁዋዌም ''ሜንግ አንዳች ስለ ፈጸመችው ስህተት የማውቀው ነገር የለም'' ብሏል።

ዛሬ አርብ ፍርድ ቤት ትቀርባለች ተብሎ ይጠበቃል።

የቻይና እና አሜሪካ የንግድ ጦርነት በተጧጧፈበት ወቅት የሜንግ እሥር ተከትሏል።

አርጀንቲና ላይ የጂ-20 ስብሰባ ወቅት ዶናልድ ትራምፕ እና የቻይናው ፕሬዚዳንት ዢ ሺፒንግ በተገናኙበት በዕለተ ቅዳሜ ነበረ ሜንግ ቫንኩቨር ካናዳ ውስጥ በቁጥጥር ሥር የዋለችው።

የሜንግ እስር ቻይናን ያስቆጠ ሲሆን በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን የንግድ ጦርነት እንዳያባብሰው ተሰግቷል።

ሜንግ በተሳረችበት ወቅት ሲወጡ የነበሩት ሪፖርቶች የእስሩ ምክንያት ምናልባትም ሁዋዌ አሜሪካ ኢራን ላይ የጣለችውን ማዕቀብ ሳይተላለፍ አልቀረም።

የአሜሪካ የአገር ውስጥ ደህንነት አማካሪው ጆን ቦልት ከእስሩ ጋር በተያያዘ ከጋዜጠኞች ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ሳይሰጡበት ቀርተዋል።

ሜንግ የኩባንያው የፋይናንስ ኃላፊ እና የሁዋዌ መስራች ልጅ ነች።

ሜንግ የኩባንያው የፋይናንስ ኃላፊ እና የሁዋዌ መስራች ልጅ ነች።

የፎቶው ባለመብት, Reuters

የምስሉ መግለጫ, ሜንግ የኩባንያው የፋይናንስ ኃላፊ እና የሁዋዌ መስራች ልጅ ነች

ሁዋዌ በዓለማችን ከሚገኙ ግዙፍ የቴሌኮም እቃዎች አቅራቢ ድርጅቶች እና አገልግሎት ሰጪዎች መካከል አንደኛው ነው። በቅርቡም ከሳምሰንግ ቀጥሎ ትልቁ ዘመናዊ ተንቀሳቃሽ ስልክ አምራች መሆን ችሏል።

የምዕራቡ ዓለም መንግሥታት ቻይና ሁዋዌን ተጠቅማ የስለላ አቅሟን ታዳብራለች ብለው ይሰጋሉ። ሁዋዌ ግን የመንግሥት ጣልቃ ገብነት የለም ይላል። የአሜሪካ ሕግ አርቃቂዎች በተደጋጋሚ ሁዋዌ የአሜሪካ ደህንነት ስጋት ነው እያሉ ይከሳሉ።

የጃፓን መንግሥት የቻይና ኩባንያ የሆኑትን ሁዋዌ እና ዜድቲኢ (ZTE) በመረጃ መረብ ደህንነት ስጋት ምክንያት በአገሪቱ ውስጥ አገልግሎት እንዳይሰጡ እገዳ ልታደርግ እንደሆነ እየተነገረ ነው። ኒው ዚላንድ እና አውስትራሊያ ሁዋዌን ካገዱ ሰነባብተዋል።