ኢራን ከሰሞኑ አሜሪካ የፈጸመችው ጥቃት "ለዲፕሎማሲ ያላትን ፍላጎት ጥርጣሬ” ውስጥ ከትቷል አለች

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
አሜሪካ እና ኢራን አንዳቸው በሌላኛቸው ላይ ጥቃት በፈጸሙ በኋላ በትናትናው ዕለት ከቱርክ አቻቸው ጋር የተነጋገሩት የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ፤ ዋሽንግተን “የተኩስ አቁም ስምምነቱን በተደጋጋሚ መጣሷ” ለዲፕሎማሲያዊ መፍትሔ ያላትን “ቁርጠኝነት ጥርጣሬ ውስጥ መክተቱን” ተናገሩ።
አራግቺ፤ ከቱርክ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሃካን ፊዳን ጋር ያደረጉት የስልክ ንግግር በዋነኛነት ትኩረት ያደረገው ቀጣናዊ ጉዳዮች ላይ እንደነበር ባወጡት መግለጫ አስታውቀዋል።
መግለጫው እንደሚያስረዳው፤ የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አሜሪካ ከሰሞኑ በፋርስ ባሕረ ሰላጤ አካባቢ “የጀብድ እንቅስቃሴ” ማድረጓን ጠቅሰዋል። “ከፍተኛ የአሜሪካ ባለሥልጣናት ጸያፍ እና ስድብ ንግግሮችን” ማድረጋቸውን በማንሳትም ከስሰዋል።
አሜሪካ እና ኢራን ሐሙስ ምሽት አንዳቸው በሌላኛቸው ላይ ጥቃት ፈጽመዋል። ጥቃቱን ማን ቀድሞ እንደጀመረው አልተረጋገጠም።
ኢራን ግን ወደ ሆርሙዝ ወሽመጥ እየተጠጉ የነበሩ ነዳጅ ጫኝ እና ሌላ መርከቧ በአሜሪካ ዒላማ እንደተደረጉባት ገልጻለች። በተለያዩ የባሕር ዳርቻ አካባቢዎች ላይ የአየር ጥቃት መፈጸሙን አስታውቃለች።
አሜሪካ በበኩሏ ወሽመጡ ላይ በሰፈረው ሚሳዔል ተሸካሚ አውዳሚ መርከቧ ላይ ኢራን ለፈጸመችባት ጥቃት “የራስን መከላከል ጥቃቶችን” በማድረስ ምላሽ መስጠቷን ትናገራለች።
የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፤ ከሰሞኑ የአሜሪካ ኃይሎች በፋርስ ባሕረ ሰላጤ “ውጥረት የማባባስ እና የተኩስ አቁም ስምምነቱን በተደጋጋሚ የመጣስ” ተግባራት ላይ መሰማራቸውን አንስተዋል።
በዚህም ምክንያት “አሜሪካ ለዲፕሎማሲው መንገድ ስላላት ፍላጎት እና ቁርጠኝነት የተፈጠረው ጥርጣሬ ጨምሯል" እንዳሉ በመግለጫው ሰፍሯል።
“የአሜሪካ አጥፊ አካሄድ የዲፕሎማሲውን ሂደት የሚጎዳ እና የኢራን ሕዝብ በአሜሪካ ዓላማ ላይ ያለውን ጥርጣሬ የሚያባብስ” እንደሆነም ተናግረዋል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ይህንን ወቀሳ ያሰሙ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አሜሪካ ላቀረበችው የስምምነት እቅድ የኢራንን ምላሽ እየጠበቁ መሆኑን በተናገሩ ማግሥት ነው። እስካሁን ድረስ ኢራን ምላሽ ስጥታ እንደሆነ አልተገለጸም።
ትራምፕ ከሐሙስ ዕለቱ ጥቃት በኋላ በማኅበራዊ ደዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ “ዛሬ በድጋሚ እንደዘረርናቸው ሁሉ፤ ስምምነታቸውን በፍጥነት ካልፈረሙ ወደፊት በበለጠ ጥንካሬ እና ከፍ ባለ ኃይል እንዘርራቸዋለን” በማለት ተናግረዋል።






















