ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ጣልያን አፍሪካን በተመለከተ የሰጠችው አስተያየት ፈረንሳይን አስቆጣ
የጣሊያን ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር ፈረንሳይ አፍሪካን ትበዘብዛለች፤ ስደትንም ታበረታታለች ማለታቸውን ተከትሎ ፈረንሳይ የጣሊያን አምባሳደርን ለጥያቄ ጠረርታለች።
እሁድ ምሽት የጣሊያን ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር ሉዊጂ ዲ ማኢኦ ፈረንሳይ በአፍሪካ ላይ ያላትን ፖሊሲ በመቃወም የአውሮፓ ህብረት ፈርንሳይ ላይ ማዕቀብ እንዲጥል ጥሪ አቅረበው ነበር።
''ፈረንሳይ ከአስር በላይ የሚሆኑ የአፍሪካ ሃገራትን ቅኝ መግዛት አላቆመችም'' ብለዋል ምክትል ጠቅላይ ሚንስትሩ።
ጣሊያን እና ፈረንሳይ ከዚህ ቀደም ስደትን የሚመለከቱ ጉዳዮች አጋጭቷቸው ነበረ። ጣሊያን ኑሯቸውን በአውሮፓ ለመመስራት ለሚጓዙ አፍሪካውያን ስደተኞች የመጀመሪያ መዳረሻቸው ነች።
ባለፈው ዓመት ፈረንሳይ ሜዲትራኒያን ባህር ላይ ጀልባቸው ችግር ላጋጠማው አፍሪካውያን ስደተኞች እርዳታ አላደረገችም በማለት ጣሊያንን ከሳ ነበረ። ጣሊያን በበኩሏ ፈረንሳይ ስደተኞችን የመቀበል ፍላጎት የላትም ብላ ነበር።
''የአውሮፓ ህብረት ፈረንሳይን እና እንደ ፈረንሳይ ያሉ አፍሪካን የሚያደኅዩ ሃገራት ላይ ማዕቀብ መጣል ይኖርበታል። ምክንያቱም አፍሪካውያን አፍሪካ ውስጥ እንጂ ከሜዲትራኒያን ባህር በታች ሆነው መገኘት የለባቸውም።''
''አፍሪካውያን አሁንም የሚሰደዱት አውሮፓዊያን ሃገራት በተለይም ፈረንሳይ በርካታ የአፍሪካ ሃገራትን ቅኝ እየገዙ ስለሆነ ነው'' ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚንስትሩ ተደምጠዋል።
የምክትል ጠቅላይ ሚንስትሩን ንግግር ተከትሎ በፈረንሳይ የጣሊያን አምባሳደር የሆኑት ቴሬሳ ካስታልዶ ለጥያቄ የፈረንሳይ የውጪ ጉዳይ ቢሮ ተጠርተዋል።
ዓለም አቀፉ የስደተኞች ተቋም እንደሚለው ከሆነ በመጀመሪያዎቹ የ2019 16 ቀናት ብቻ ከአራት ሺህ በላይ ስደተኞች በባህር ተጉዘው አውሮፓ ደርሰዋል። ይህም አሃዝ ከአንድ ዓመት በፊት ከነበረው ጋር ሲነጻጸር በእጥፍ ጨምሯል ብሏል ተቋሙ።