ኪም ጆንግ-ኡን ሌሎች አማራጮችም አሉ ሲሉ አስጠነቀቁ

የሰሜን ኮሪያው መሪ ኪም ጆንግ-ኡን የኒውክሌር ማበልጸግ ሥራቸውን ለመግታት ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸው፤ ሆኖም አሜሪካ በሰሜን ኮሪያ ላይ የጣለችውን ማዕቀብ የማታነሳ ከሆነ በኒውክሌር ፕሮግራሙ እንደሚገፉበት አሰጠንቅቀዋል።

ኪም ጆንግ-ኡን ይህን ያሉት በስፋት ሲጠበቀ በነበረው የአዲስ ዓመት መልዕክታቸው ነው።

ባሳለፍነው ሰኔ ኪም ጆንግ-ኡን ከፕሬዚዳንት ትራምፕ ጋር ፊት ለፊት ተገናኝተው ቢወያዩም የውይይታቸው ውጤት እምብዛም ነው።

ሰሜን ኮሪያ የአሜሪካ ግዛቶችን መምታት የሚችሉ ሚሳኤሎችን ከሞከረች በኋላ ነበር የአሜሪካ ባለስልጣናት ከኪም ጆንግ-ኡን ጋር ፊት ለፊት ለመገናኝት እንደ አዲስ ጥረት ማድረግ የጀመሩት።

ኪም ጆንግ-ኡን በአዲስ ዓመት ንግግራቸው ''አሜሪካ በመላው ዓለም ፊት የገባችውን ቃል የማታከብር ከሆነ እና በሰሜን ኮሪያ ላይ የተጣለውን ማዕቀብ የማታነሳ ከሆነ፤ የሚኖረን ምርጫ በራሳችን መንገድ የሪፓብሊኩን ሉዓላዊነት እና ጥቅም ለማስከበር አዲስ አማራጮችን መፈለግ ነው'' ብለዋል።

ሰሜን ኮሪያ በተባበሩት መንግሥታት የጸጥታ ምክር ቤት ዘረፈ ብዙ ማዕቀቦች ተጥለውባታል።

ኪም ጨምረው እንደተናገሩት ሰሜን ኮሪያ የኒውክሌር መሳሪያዎችን እንደማትሰራ፣ እንደማትጠቀም እና እንዲሁም እንደማታስፋፋ በገባችው ቃል መሰረት፤ ጉልህ እርምጃዎች ተወስዷል ብለዋል።

በተጨማሪም ኪም ከፕሬዚዳንት ትራምፕ ጋር ዳግመኛ በማንኛውም ሰዓት ፊት ለፊት ለመገናኘት ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል።

ፕሬዚዳንት ትራምፕ በበኩላቸው ከአንድ ወር በኋላ ከኪም ጋር ሊገናኙ እንደሚችሉ ጠቁመዋል።

ኪም እና ትራምፕ ሲገናኙ፤ የሰሜን ኮሪያ መሪ በስራ ላይ ከሚገኝ ከአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጋር ፊት ለፊት ሲገናኝ ለመጀመሪያ ጊዜ ነበር። ሁለቱ መሪዎች ባደረጉት ውይይት ሰሜን ኮሪያ የኒውክሌር ማበልጸግ ስራዋን እንድታቆም የሚያስችል ሥራዎችን ለመስራት ከስምምነት ደርሰናል ብለው ነበር።

ከሁለቱ መሪዎች ግንኙነት በኋላ ሰሜን ኮሪያ የሚሳኤል እና የኒውክለር ሙከራዎችን አቁማለች።