ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ካለሁበት 40: "ካለ ቪዛ ወደ 127 አገራት መጓዝ እችላለሁ"
ለቲ ሂርጳ እባላለሁ። ምዕራብ ወለጋ ጊዳ አያና የምትባል ከተማ ውስጥ ነው ተወልጄ ያደግኩት።
ከአገር ከወጣሁ 15 ዓመታት አልፉ፤ አሁን የምኖረው ካናዳ ኤድመንተን በምትባል ከተማ ውስጥ ነው።
የመጀመሪያ ዕቅዴ አሜሪካ ወደሚኖረው ወንድሜ ጋር መሄድ ነበር። ወንድሜም አሜሪካ እንዲወስደኝ ዕድሎችን ለማመቻቸት 1996 ላይ ወደ ኬንያ አቀናሁ።
ይሁን እንጂ የወንድሜ ጥረት ሳይሳካ ቀረ፤ እኔም ወደ ኢትዮጵያ አልመለስም ብዬ ኬንያ ጥገኘነት ጠይቄ መኖር ጀመርኩ።
አንድ በር ሲዘጋ ሌላው ይከፈታል እንደሚባለው ሁሉ፤ ሌላ መልካም ዕድል አጋጥሞኝ ወደ ካናዳ መጣሁ።
ኢትዮጵያን እና ካናዳ በሰፊው ከሚለያዩበት አንዱ ደህንነት ነው።
እዚህ አገር ምን ሰርቼ እራሴን ላኑር የሚለው ነገር ነው ሰውን የሚያስጨንቀው እንጂ የግል ደህንነቱ አያሳስበውም።
እዚህ ከመጣሁ በኋላ ብዙም የከበደኝ ነገር አልነበረም። የመጣሁ ሰሞን በረዶ የሚጥልበት ወቅት ስለነበር ቅዝቃዜው ከብዶኝ ነበር።
ከአገር የሚናፍቀኝ ነገር ቢኖር ማህበራዊ ህይወቱ ነው። ኢትዮጵያ ውስጥ ሰዉ ተሰባስቦ አብሮ በልቶ መጨዋወት የተለመደ ነገር ነው። እዚህ አገር ግን ይህን አይነት ልማድ የለም።
አገር ቤት ጎረቤት ዘመድ ነው። እዚህ አገር ግን ጎረቤቴ ማን እንደሆነ አንኳ አላውቅም።
እዚህ አገር መልካም የሆነልኝ የካናዳ ዜግነት ማግኘቴ እና የአገሪቱ ዜጎች ያላቸውን መብት እኔም መጋራቴ ነው።
የካናዳ ዜግነት ማግኘቴ ቪዛ ሳያስፈልገኝ 172 አገራትን መጎብኘት ያስችለኛል።
የህንድ ምግብ በጣም እወዳለሁ። ከቤት ውጪ ከተመገብኩ 'ቺክን ብራይን' የተባለውን ምግብ መመገብ እመርጣለሁ።
በልጅነቴ ወንዝ ውስጥ ስዋኝ እና ለጫካ ቅርብ ሆኜ በማደጌ እዚህ አገር ደን እና የውሃ አካል ባየው ቁጥር አገሬን ያስታውሰኛል።
በተለይ ደግሞ የምኖርባትን ኤድመንተን ከተማ ለሁለት ከፍሎ የሚያልፍ ሳሰኬቹዋን የሚባለውን ወንዝ አገሬን ያስታውሰኛል።
የካናዳ የአየር ጸባይ፤ በበጋ ወቅት እጅግ ሞቃታማ እንዲሁም በቅዝቃዜ ወቅት እጅግ ቀዝቃዛ ነው የሚሆነው።
ለፊራፍኦሊ ዱጋሳ እንደነገራት
የ'ካለሁበት' ቀጣይ ክፍሎችን ለማግኘት ፦