የጦርነት ውጥረት በነገሠባት ሊባኖስ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በምን ሁኔታ ውስጥ ይገኛሉ?

የመካከለኛው ምሥራቅ ውጥረት እየተባባሰ ከመምጣቱ ጋር በተያያዘ ብዙ አገራት ዜጎቻቸው ከሊባኖስ ለቀው እንዲወጡ ማሳሰቢያ ሰጥተዋል።

የሐማስ የፖለቲካ መሪ ኢስማዔል ሃኒያ መገደላቸውን ተከትሎ ኢራን እስራኤል “ከፍተኛ ቅጣት” ይጠብቃታል ስትል ዝታለች።

ኢስማዔል ሐኒያ ከመገደላቸው ከሰዓታት በፊት በሊባኖስ ኃያሉ ወታደራዊ እና የፖለቲካ ቡድን የሆነው የሄዝቦላህ ከፍተኛ ኮማንደር ፉዓድ ሹክር በመዲናዋ ቤሩት በእስራኤል የአየር ጥቃት ተገድሏል።

በከተከታታይ የሄዝቦላህ መሪዎች ላይ ግድያ መፈጸሙ፣ ሄዝቦላህ በእስራኤል ድንበር አቅራቢያ ባደረሰው ጥቃት ሰዎች በመሞታቸው እና በኢራን እና በእስራኤል መካከል ያለው ውጥረት ከመቼውም በላይ በመባባሱ ምክንያት በሊባኖስ ውጥረት ነግሷል።

ኢራን የምትደግፈው ሄዝቦላህ በኢራን የበቀል ጥቃት ውስጥ ጉልህ ሚና እንደሚኖረው እና ለዚህ የበቀል ጥቃት የእስራኤል ምላሽ መካከለኛው ምሥራቅን ወደተባባሰ ቀውስ ሊመራው ይችላል ተብሎ ተሰግቷል።

በርካታ ስደተኛ ኢትዮጵያውያን ከሚኖሩባት ሊባኖስ/ቤይሩት ዜጎቻቸው እንዲወጡ አሜሪካ፣ ዩናይትድ ኪንግደም፣ አውስትራሊያ፣ ፈረንሳይ፣ ካናዳ፣ ደቡብ ኮሪያ፣ ሳዑዲ አረቢያ፣ ጃፓን፣ ቱርክ፣ ዮርዳኖስ እና ሌሎችም አገራት ማስጠንቀቂያ ሰጥተዋል።

“የሌሎች አገር ዜጎች ሲወጡ የእኛ አገር ሰዎች ግን እየገቡ ነበር”

በሊባኖስ የኢትዮጵያውያን በጎ አድራጎት ድርጅት የሆነው ‘እኛ ለእኛ በስደት’ ምክትል ዳይሬክተር እና በቤሩይት ነዋሪ የሆነችው እኑ፣ በተለይም በደቡብ ሊባኖስ አካባቢ የሚኖሩ ሰዎች “በፍራቻ ውስጥ እየኖሩ ነው” ስትል ለቢቢሲ ትገልጻለች።

ከዚህ ቀደም ሄዝቦላህ በእስራኤል ይዞታ ሥር ባለው የጎላን ተራራ አካባቢ በፈጸመው የሮኬት ጥቃት 12 ሕጻናት እና ታዳጊዎችን ገድሏል ስትል እስራኤል ከሳለች።

በአካባቢው በየቀኑ የተኩስ ልውውጥ መኖሩ በሁለቱ ወገኖች መካከል የለየለት ጦርነት ሊነሳ ይችላል የሚል ስጋት አጭሯል።

እኑ፣ በደቡብ ሊባኖስ ያለው ውጥረት በጋዛ ካለው ውጊያ ጋር በተመሳሳይ ጊዜ መጀመሩን ትናገራለች።

“ከዚያ አካባቢ ከ90 ሺህ በላይ ሕዝብ ተፈናቅሏል። ሃበሾችም አሉበት። አንዳንድ መጥፎ አሠሪዎች ቤታቸውን ለቀው በሚሄዱበት ጊዜ ሠራተኞቻቸው ላይ ቆልፈው ሄደዋል” ትላለች።

የተባበሩት መንግሥታት እንዳለው በደንበር አካባቢ እየተፈጸሙ ባሉ ጥቃቶች ሳቢያ ከሊባኖስ 90 ሺህ ሰዎች ተፈናቅለዋል። በተጨማሪም 100 ንጹሀን ዜጎች እና 366 የሄዝቦላህ ታጣቂዎች በእስራኤል ጥቃት ተገድለዋል።

የእስራኤል ባለሥልጣናት እንደሚሉት፣ በሄዝቦላህ ጥቃት ምክንያት 60,000 ሰዎች ሲፈናቀሉ 10 ሰላማዊ እስራኤላውያንን ጨምሮ 33 ሰዎች ተገድለዋል።

“የሌሎች አገር ዜጎች ሲወጡ የእኛ አገር ሰዎች [ኢትዮጵያውያን] ግን እየገቡ ነበር። ይህ መሆን አልነበረበትም” ስትል እኑ ያለውን ሁኔታ ትገልጻለች።

“እዚህ አገር ብዙ የኖርነውም የተነገረን ነገር የለም። የሆነ ነገር ቢፈጠር እንኳን ተብሎ መጠለያ አልተዘጋጀም” ትላለች።

ከአካባቢው መውጣት ስለሚቻልበት መንገድ እና የቅድመ ጥንቃቄ መልዕክትን በተመለከተ ከኢትዮጵያ ኤምባሲ የሰሙት ነገር እንደሌለ ትናገራለች።

“ሁሉም ሰው በያለበት በፍርሃት ውስጥ ነው የሚኖረው። ፍንዳታ ስንሰማ ምን ሆነ? ምን ተፈጠረ? እያልን እየደነገጥን ነው ያለነው” ብላለች እኑ።

ሄዝቦላህ እና እስራኤል እአአ በ2006 ያካሄዱት ጦርነት 18 ዓመት የሞላው ሲሆን፣ አሁን ደግሞ ለወራት ዝግ ባለ ሁኔታ ሲካሄድ የነበረው ጦርነት ወደ አዲስ ሁሉን አቀፍ ጦርነት ሊሸጋገር የሚችልበት አጋጣሚ ተፈጥሯል።

ነገሮች እየተባባሱ ከሄዱ የበጎ አድራጎት ድርጅቱ ‘እኛ ለእኛ በስደት’ የከፋ ሁኔታ ውስጥ ላሉ ኢትዮጵያውያን መጠለያ ለመከራየት እንቅስቃሴ እያደረገ እንደሆነ ምክትል ዳይሬክተሯ እኑ ገልጻለች።

ኢትዮጵያውያን ሊባኖስን ለቀው እየወጡ እንደሆነ ተጠይቃ “ሥራ አለ፤ ብድግ ብለው መሄድ የሚችሉ ሰዎች አይደሉም። ግን መሄድ እየፈለጉ ያልቻሉ አሉ። ክስ ይኖርባቸዋል፣ ወረቀት የላቸውም፣ የትኬት ገንዘብ ላይኖራቸው ይችላል። የትኬት ገንዘብ ቢኖራቸው እንኳን ‘ቤሩይት ታስፈራለችና ልሂድ’ ማለት አይችሉም” ስትል ያለውን አስቸጋሪ ሁኔታ ለቢቢሲ ተናግራለች።

በእስራኤልና በሄዝቦላህ መካከል ያሉት የድንበር አካባቢ ግጭቶቹ እንዳሉ ሆነው ሁለቱም ወገኖች ወደለየለት ጦርነት የሚወስዳቸውን መስመር ላለማለፍ እየሞከሩ እንደሚገኙ ባለፈው ሳምነት የወጡ ሪፖርቶች ጠቁመዋል።

በዚህ ሳምንት ግን ነገሮች ከቁጥጥር ውጪ ሊወጡ ይችላሉ የሚል ስጋት አንዣቧል።

የሄዝቦላህ ከፍተኛ ኮማንደር ፉዓድ ሹክር በሊባኖስ መዲና ቤሩት በእስራኤል ኃይሎች መገደሉን ተከትሎ፣ ሄዝቦላህ የበቀል እርምጃ ለመውሰድ ዝቷል።

በቅርቡ ሄዝቦላህ አያልት ሀሻሀር በተባለ የእስራኤል ሰሜናዊ አካባቢ የድሮን ጥቃት መፈጸሙን ሲያሳውቅ፣ የእስራኤል መከላከያ ሁለት ወታደሮች እንደሞቱ ገልጿል።

ሄዝቦላህ ከዚህ ጥቃት በፊት ቤይት ሂለል በተባለ አካባቢ የሮኬት ጥቃት ሲፈጽም፣ የእስራኤል አየር ኃይል በምላሹ በደቡባዊ ሊባኖስ ጥቃት አድርሷል።

ከእስራኤል ጋር በሚያዋስን ድንበር አካበቢ፣ ሜይስ አል-ጃባል በተባለው ከተማ በደረሰው ጥቃት የሄዝቦላህ ተዋጊና የሕክምና ባለሙያ ተገድለዋል።

“ልጄ ‘ማታ ተኩስ ይኖራል?’ ብላ ትጠይቀኛለች”

ሌላዋ በደቡባዊ ሊባኖስ፣ የምትኖረው ኢትዮጵያዊት ትዝታ ለገሰ፣ ሮኬቶች በተደጋጋሚ በሚወረወሩበት ወቅት የቤት መነቃነቅ እንደሚሰማቸው ገልጻ፣ በድንጋጤ ውስጥ እንደሚገኙ ለቢቢሲ ተናግራለች።

“እኔ ልጅ አለችኝ። የሮኬት ተኩስ የሚመጣው ሳናስበው ስለሆነ ከድንጋጤ የተነሳ ምንም የምናደርገው ነገር የለም። ወይ ሮጦ መውጣት ወይ በእጅ የያዙትን መልቀቅ ሊኖር ይችላል” ስትል ሁኔታውን ገልጻለች።

ልጇ ለመጀመሪያ ጊዜ የሮኬት ተኩስ ድምጽ የሰማችው ትምህርት ቤት ሳለች እንደነበር የምትናገረው ትዝታ፣ “ጓደኞቿ ሁሉ ሲሯሯጡ እሷ በድንጋጤ እነሱን ታይ ነበር። ቤት መጥታ ግን ስቅስቅ ብላ ነው ያለቀሰችው” ትላለች።

“እዚያ ራሴን እንደ ጠንካራ አይቼው እዚህ ስመጣ ግን ፈራሁ ብላ ልጄ ስታለቅስ ነበር” ስትል የተከሰተውን ትገልጻለች።

ልጇ ‘ማታ ተኩስ ይኖራል?’ ብላ እንደምትጠይቃት እና እሷም ልጇን ላለማስጨነቅ ስትል ‘የለም’ ብላ እንደምትመልስ ተናግራለች።

አሁን ባለው ሁኔታ ስጋታቸው “ጦርነት እንዳይነሳ” እንደሆነ ትዝታ ገልጻለች።

ኢራን እና በኢራን የመደገፈው የሊባኖሱ ሄዝቦላህ በእጅጉ ያስቆጣቸው ጥቃት ባለፈው ሳምንት በእስራኤል ተፈጽሞባቸዋል። ይህንንም በአስራኤል ላይ የቀጥታ ጥቃት በመፈጸም እንደሚበቀሉት በይፋ እየተናገሩ ነው።

ይህ ከሆነ ደግሞ እስራኤል በተለይ በድንበር በምትዋሰናት ሊባኖስ ውስጥ ከሚገኘው ሄዝቦላህ ጋር ወደ ሙሉ ጦርነት ልትገባ እንደምትችል እየተነገረ ነው።

የኢራን ተጠባባቂ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አሊ ባከሪ ካኒ ከአውሮፓ ኅብረት የውጭ ፖሊሲ ኃላፊ ጆሴፍ ቦሬል ጋር በስልክ በተወያዩበት ጊዜ አገራቸው “ያለጥርጥር ሕጋዊ እና ተፈጥሯዊ መብቷን በመጠቀም” እስራኤልን ትቀጣለች ብለዋል።

ባለፈው አርብ የአራን መንግሥት ቴሌቪዥን አቅራቢ “ዓለም ከዚህ በፊት አጋጥሞት የማያውቀው የተለየ ነገርን ይመለከታል” ሲል አስጠንቅቆ ነበር።

የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታኒያሁ ባደረጉት ንግግር “ከሁሉም አቅጣጫ ዛቻዎች እየተሰነዘሩብን ነው . . . ፈታኝ ቀናት ከፊታችን ይጠብቁናል። ለማንኛውም ሁኔታ ዝግጁ ነን” ሲሉ ዜጎቻቸውን አስጠንቅቀዋል።

አሜሪካ እና ዩናይትድ ኪንግደም ዜጎቻቸውን ከሊባኖስ እንዲወጡ ከማዘዛቸው በተጨማሪ ወደ አካባቢው የጦር መርከቦቻቸውን እና ወታደራዊ አማካሪዎቻቸውን እያሰማሩ ነው።

ወትሮም በሊባኖስ በፈታኝ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙት ኢትዮጵያውያን ባሉባቸው የተለያዩ ችግሮች ምክንያት ፈጣሪ ሰላም እንዲያወርድ ከመለመን ውጪ አማራጭ ያላቸው አይመስሉም።