የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት ራማፎሳ በሌሎች አፍሪካውያን ላይ በደረሰው ጥቃት ማፈራቸውን ገለፁ

የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት ሲሲል ራማፎሳ በቅርቡ መጤ ጠል በሆኑ የአፍሪካ ዜጎች ላይ የደረሰው ጥቃት እጅግ አድርጎ እንደሚያሳፍራቸው ለቢቢሲ ተናግረዋል።

የንግድ መናሃሪያ በሆነችው ጆሃንስበርግ መተዳደሪያቸው ንግድ የሆኑ ከሌሎች አፍሪካ አገር የመጡ ዜጎች ላይ የተደራጁ ቡድኖች ጥቃት አድርሰውባቸዋል፤ ንብረታቸውም ወድሟል። ጥቃቱ በሌሎችም ከተሞች ቀጥሎ ለብዙ ቀናት ቀጥሎ ነበር።

የሃገሪቱ ባለስልጣን እንደገለፁት አስራ ሁለት ሰዎች ሲገደሉ፤ ከነሱም መካከል አስሩ ደቡብ አፍሪካውያን ናቸው ብለዋል።

የቢቢሲው ዘጋቢ ሚልተን ኒኮሲ ፕሬዝዳንቱ "በጥቃቱ አፍረዋል ወይ ብሎ" ለጠየቃቸው ጥያቄ ሲመልሱ፤ "እንዴት አላፍርም፤ እኛ ደቡብ አፍሪካዊያን በአፓርታይድ ጊዜም ሆነ ከዚያ በኋላ ብዙ አገሮች አስጠልለውን እኛ በምላሹ እነሱን ስናጠቃ እንዴት አላፍርም" ብለዋል።

አክለውም " ይህ ደቡብ አፍሪካ ከምትቆምበት እሴት የሚፃረር ነው፤ ህዝባችን ሌሎች የአፍሪካ ዜጎችን አይጠላም። አሁንም ቢሆን የሌሎች አገር ዜጎች መጥተው መስራት ይችላሉ። ዜጎቻችንም የሃገሪቱን ህግ እንዲያከብሩ እንፈልጋለን" ብለዋል።

ራማፎሳ ደቡብ አፍሪካ ውስጥ አሁንም ቢሆን የአፍሪካውያንነትና የፓን አፍሪካዊነት መንፈስ እንዳለም ለማስረዳትም መልዕክተኞችን ወደ ሰባት ሃገራት ልካለች።

በቅርቡ የደረሰው ጥቃት ደቡብ አፍሪካ በአህጉሪቷ ላይ ያለውን ስሟን አጠልሽቶታል።

በዚምባብዌ መዲና ሐራሬ ለቀድሞው ፕሬዚዳንት ስርአተ ቀብር የተገኙት ራማፎሳ ንግግር በሚያደርጉበትም ወቅት ከዚምባብዌውያን ዘንድ ተቃውሞ ገጥሟቸዋል።