ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ኔታንያሁ እስራኤል ዋይት ኃውስን ትሰልላለች የሚለውን ዘገባ አስተባበሉ
የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንጃሚን ኔታንያሁ፤ አገራቸው አሜሪካን ትሰልላለች ተብሎ የወጣውን ዘገባ ሙሉ በሙሉ አስተባበሉ።
እስራኤልን አሜሪካን በመሰለል የሚወነጅለው ዘገባ በአሜሪካ በሚገኝ 'ፖለቲኮ' በተሰኘ የዜና ድረገፅ ላይ የወጣው ሐሙስ ዕለት ነበር።
'ፖለቲኮ' የተሰኘው ይህ የዜና ድረገፅ፤ ሦስት የቀድሞ የአሜሪካ ከፍተኛ ባለስልጣናትን ጠቅሶ፤ ዋይት ኃውስ አቅራቢያ ተገኘ ካለው የመከታተያ መሣሪያ ጀርባ እስራኤል ትኖርበታለች ሲል ዘግቧል።
ነገር ግን ከጠቅላይ ሚኒስትር ኔታንያሁ ቢሮ የወጣው መግለጫ እንደሚያስረዳው ውንጀላው "ነጭ ውሸት ነው"።
"በአሜሪካ በየትኛውም የስለላ ተግባር ላለመሳተፍ ረዥም ጊዜ ፀንቶ የቆየ መግባባት እና አሠራር አለ" ይላል መግለጫው አክሎ።
ሐሙስ ዕለት ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በጋዜጠኞች ስለ ሪፖርቱ ሲጠየቁ፤ እስራኤል አሜሪካን ትሰልላለች ብለው እንደማያምኑ ተናግረው ነበር።
"እጅጉን ለማመን ተቸግሬያለሁ፤ ከእስራኤል ጋር ያለኝ ግንኙነት በጣም ጥሩ ነው" ያሉት ፕሬዝዳንት ትራምፕ፤ ከኢራን ጋር ያለው የኒውክሌር ስምምነት ማብቃቱንና አሜሪካ በእስራኤል የሚገኘውን ኢምባሲዋን ወደ እየሩሳሌም ለማዞር የወሰነችበትን አወዛጋቢ ውሳኔ በአስረጅነት ጠቅሰዋል።
"ይህንን ወሬ አላምነውም፤ አይሆንም ማለት አልችልም፤ ግን አላምንም" ብለዋል።
'ፖለቲኮ' የተሰኘው ድረገፅ በዘገባው ላይ እንዳስቀመጠው፤ የእስራኤል ሞባይል ኔትወርክ አቅራቢ ስቲንግሬይስ፣ ንብረት የሆነ መሣሪያ በፕሬዝዳንቱ መኖሪያ አቅራቢያ የተገኘ ሲሆን፤ ከዚህ በፊትም በትራምፕ አስተዳደር ዘመን ዋሺንግተን ዲሲ አቅራቢያ ሌላ ተመሳሳይ መሣሪያ መገኘቱን ጠቅሷል።
ይህ መሣሪያ እንደ ሞባይል ኔትወርክ ማማ የሚመስል ሲሆን፤ ስልኮችን በመጥለፍ ያሉበትን ሥፍራ፣ የማን እንደሆኑ፣ እንዲሁም መደወልና ዳታቸውን መጠቀም ያሰችላል።
ስማቸው እንዲገለፅ ያልፈለጉ የቀድሞ ባለስልጣን ለዜና ተቋሙ እንዳሉት፤ ስቲንግሬይስ ይህንን መሣሪያ የሠራው ሆን ብሎ ፕሬዝዳንት ትራምፕን ለመሰለል ነው። ነገር ግን ይሳካላቸው አይሳካላቸው ማረጋገጥ አለመቻላቸውን ጠቅሰዋል።
የአሜሪካው የፌደራል ወንጀል ምርመራ ቢሮ (ኤፍቢአይ) ፀረ ስለላ ቡድን መሣሪያው ከየት እንደመጣ ማጥናቱን የጠቀሱት የአሜሪካ የስለላ መሥሪያ ቤት የቀድሞ ባለስልጣን፤ "የእስራኤል እጅ እንዳለበት ግልፅ ነው" ብለዋል ለ'ፖለቲኮ'።
እኚሁ ባለስልጣን የትራምፕን አስተዳደር የተቹ ሲሆን፤ የእስራኤል መንግሥትን በይፋም ይሁን በግል ስለላ በማካሄዳቸው አለመውቀሳቸውን ኮንነዋል።
"ማንም ተጠያቂ ስለመደረጉ አልሰማሁም" ብለዋል እኚህ የቀድሞ ባለስልጣን።
የኔታንያሁ ማስተባባል እንዳለ ሆኖ፤ እስራኤል ከዚህ ቀደም አሜሪካን ሰልላ ታውቃለች።
ራፊ ኢታን፣ በ1960 ናዚ አዶልፍ ኢችማንን በቁጥጥር ሥር ያዋለው የሞሳድ ወኪል፣ በ1980 በርካታ ከፍተኛ ሚስጥር የያዙ የአሜሪካ ሰነዶችን ለእስራኤል ማስተላለፉን ይፋ አውጥቶ ተናግሮ ነበር።
በ2006 ደግሞ የአሜሪካ መከላከያ ኃይል ተቀጣሪ የነበረው ሎውረንስ ፍራንክሊን የአሜሪካን ጥብቅ ሚስጥር የያዙ ሰነዶችን ለእስራኤል አሳልፎ በመስጠቱ የ13 ዓመት እስራት ተፈርዶበታል። በኋላ ላይ እስሩ በአስር ወር የቁም እስር ተቀይሮለታል።