ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ደቡብ አፍሪካዊቷ የፓርላማ አባል የዘረኝነት ጥቃት ደረሰባት
ደቡብ አፍሪካዊቷ የተቃዋሚ ፓርቲው የዲሞክራቲክ አሊያንስ ቃል አቀባይና የፖርላማ አባሏ ፑምዚሌ ቫን ዳሜ በኃገሪቱ ውስጥ አሉ ከሚባሉት የቱሪስት መናኸሪያ አንዱ በሆነው 'ቪኤ ዋተር ፍሮንት' በተሰኘው ስፍራ የዘረኝነት ጥቃት እንደደረሰባት ገልፃለች።
ፑምዚሌ ቫን ዳሜ በኬፕታውን ከተማ 'ቪኤ ዋተር ፍሮንት' የተባለውን ቦታ እየጎበኘችበት በነበረችበት ወቅት አንዲት ነጭ ሴት እንደሰደበቻት በትዊተር ገጿ አስፍራለች።
ስድቡ ምን እንደሆነ ግልፅ ያልተደረገ ሲሆን ነጯ ሴት ይቅርታ ጠይቂ ብትባልም በእምቢተኝነቷ እንደፀናች የፓርላማ አባሏ ገልፃለች።
"ከስፍራው በወጣሁበትም ወቅት ውጭ ላይ ሴትዮዋ ከቤተሰቦቿ ጋር ተሰባስባ በሚያስፈራራ መልኩ እያየችኝ ነበር፤ እናም ለምንድን ነው እንዲህ የምታይኝ ብየ ስጠይቃትም፤ ጥቁር ስለሆንሽ ነው የሚል መልስ ሰጥታኛለች" ብላለች።
ሴትዮዋ ብቻ ሳትሆን ልጇም እንደሰደባትና ጥቁር ስለሆነችም መሳደብ እንደሚችል የነገራት ሲሆን እየቀረፀችበት የነበረውንም ስልኳን መሬት ላይ በመወርወሩ ራሷንም ለመከላከል በቦክስ እንደመታችው ተናግራለች።
በቦታው የነበረው የጥበቃ አካል እንዳልደረሰላትም መግለጿን ተከትሎ የቦታው አስተዳደር በተገቢው መልኩ ምላሽ ባለመስጠታቸው ይቅርታ ጠይቀው ምርመራ እንደሚጀመር ገልፀዋል።