በኒውዚላንዱ የመስጊዶች ጥቃት 50 ሰዎች ተገደሉ

ዛሬ በኒውዚላንድ ክሪስትቸርች ከተማ ሁለት መስኪዶች ላይ በተከፈተ ተኩስ 49 ሰዎች ሲገደሉ ብዙዎች መጎዳታቸውን ፖሊስ አስታውቋል።

ጥቃቱን ፈፅሟል የተባለ አንድ ታጣቂ ነገ ፍርድ ቤት ቀርቦ ክስ እንደሚመሰረትበትም ተገልጿል።

ግለሰቡ ጭንቅላቱ ላይ አድርጎ በነበረው ካሜራ አልኑር በተባለው መስጊድ ሕፃን፣ ሴት ሳይል በመስጊዱ የነበሩ ሰዎች ላይ ሁሉ የተኩስ እሩምታ ሲከፍት በፌስቡክ ቀጥታ ማሰራጨቱም ተገልጿል።

ቀደም ሲል በጥቃቱ እጃቸው አለበት ተብሎ የተጠረጠሩ ሦስት ወንዶችና አንዲት ሴት በቁጥጥር ሥር መዋሉን ፖሊስ ገልፆ የነበረ ቢሆንም ኋላ ላይ ግን አንደኛው ግለሰብ ከጥቃቱ ጋር ምንም ግንኙነት የለውም በሚል ተለቋል። የቀሪዎቹ ተጠርጣሪዎች ጉዳይ እያጣራ እንደሆነም ፖሊስ አስታውቋል።

የኒውዚላንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ጃሲንዳ አርደርን ጥቃቱ የተፈፀመበት ይህ ቀን የአገሪቱ "ጨለማ ቀን" ነው ብለዋል።

የአውስትራሊያ ጠቅላይ ሚኒስትር ስኮት ሞሪሰን ደግሞ በቁጥጥር ሥር ከዋሉት አንዳቸው አውስትራሊያዊ መሆናቸውን አስታውቀዋል።

ተጠርጣሪዎቹንም "ፅንፈኞች፣ ቀኝ ዘመም አሸባሪዎች" ብለዋቸዋል።