ፕሬዚዳንት ፑቲን በዩክሬን ላይ ወታደራዊ ዘመቻ እንዲካሄድ ትዕዛዝ ሰጡ

የሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን በምስራቃዊ ዩክሬን ዶንባስ ክልል ወታደሮቻቸው ልዩ ወታደራዊ ዘመቻ እንዲያካሂዱ ትዕዛዝ ሰጥተዋል።

ፕሬዝዳንቱ በቴሌቪዥን ባስተላለፉት መልእክት በሩሲያ የሚደገፉ አማጺያኖች ጋር እየተዋጉ የሚገኙ የየክሬን ወታደሮች መሳሪያቸውን አስቀምጠው ወደቤታቸው እንዲመለሱ ጥሪ አስተላልፈዋል።

ፕሬዝዳንቱ አክለውም ዩክሬንን የመቆጣጠር እቅድ እንደሌላቸው የገለጹ ሲሆን ነገር ግን ማንኛውም አካል ሩሲያ ላይ አደጋ የሚጭር ነገር ካደረገ ምላሻችን ፈጣን ነው ብለዋል።

ዩክሬን ደግሞ ፕሬዝዳንት ፑቲን አገሪቱን ሙሉ በሙሉ ለመውረር እንቅስቃሴው ተጀምሯል ብላለች።

የዩክሬኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዲሚትሮ ኩሌባ በትዊተር ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት መልዕክት ''ሰላማዊ የሆኑ የዩክሬን ከተሞች ጥቃት እየደረሰባቸው ነው። ይህ ጦርነት መጎሰም ነው። ዩክሬን እራሷን ትከላከላለች፤ ስትከላከልም ቆይታለች። ዓለም ፑቲንን ሊያስቆመው ይገባል። እርምጃ ለመውሰድ ጊዜው አሁን ነው'' ብለዋል።

እየወጡ ባሉ ሪፖርቶች መሰረት አንዳንድ የዩክሬን ከተሞች ውስጥ ተኩስና ፍንዳታ የሚሰማ ሲሆን በዋና ከተማዋ ኪዬቭ በሚገኘው ቦሪስፒል አየር ማረፊያ አካባቢም ተኩስ እየተሰማ ስለመሆኑ ሪፖርቶች እየወጡ ነው።

የአሜሪካው ፕሬዝደንት ጆ ባይደን እና አጋሮቻቸው የሩሲያን እንቅስቃሴ ተከትሎ የተለያዩ ማዕቀቦችን የጣሉ ሲሆን ከዚህ ከበድ ያሉ ማዕቀቦች እንደሚቀጥሉ ገልጸው ነበር።

''ፕሬዝደንት ፑቲን ቀድሞ የተዘጋጀበትን ጦርነት ለማካሄድ ቆርጧል። ይህ የሚሆን ከሆነ የሚደርሰው ሰብአዊ እና ቁሳዊ ኪሳራ ከፍተኛ ነው። ዓለም ፑቲንን ተጠያቂ ታደርጋለች'' ሲሉ ተደምጠዋል ፕሬዝደንት ጆ ባይደን።

የሩሲያው ፕሬዝዳንት ይህንን መልዕክት በቴሌቪዥን ይፋ ከማድረጋቸው በፊት የዩክሬኑ ፕሬዝዳንት ቮሎደሚር ዜሌንስኪ ሩሲያ አውሮፓ ውስጥ ከፍተኛ ጦርነት ልትጀምር እንደምትችል በመግለጽ ሩሲያውያን ይህንን እንዲቃወሙ አሳስበዋል።፥

ፕሬዝዳንቱ እንዳሉት ቢያንስ 200 ሺ የሚሆኑ የሩሲያ ወታደሮችና በሺዎች የሚቆጠሩ የጦርነት ተሽከርካሪዎች ዩክሬን ድንበር ላይእንደሚገኙ ገልጸዋል።

ሩሲያ በምስራቃዊ ዩክሬን የሚገኙት ዶንቴስክ እና ሉሀንስክ ለተባሉት ክልሎች እውቅና ከሰጠች በኋላ ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ወታደሮቻችንን የላክነው "ሰላም ለማስከበር ነው" ብለዋል።

ይህንን ተከትሎም ጀርመን ከሩሲያ ወደ አውሮፓ ነዳጅ የሚያስተላልፈውን ግዙፍ ትቦ ሥራ አቋርጣለች። አሜሪካም ብትሆን ጦሯን በሩሲያ አቅራቢያ ወደሚገኙት የሰሜን አትላንቲክ ጦር ቃልኪዳን (ኔቶ) አባል አገራት ኢስቶኒያ፣ ላቲቪያ እን ሊቱኒያ እያስጣጋች ነው።

ጣልያንም ተዋጊ ጀቶችና ሄሊኮፕተሮችን ጨምሮ በፖላንድ ጦር እያሰፈረች ትገኛል።

ዩክሬን 44 ሚሊዮን ህዝብ ያላት ሲሆን ከሩሲያ እና የአውሮፓ ህብረት ጋር ድንበር ትጋራለች። አማጺያን በሚቆጣጠሯት ዶኔስክ ታንኮች መግባታቸውን የሚገልጹ ዘገባዎች አሉ። የቅርብ ጊዜ የሳተላይት ፎቶዎች ደግሞ የሩስያ ጦር ከዩክሬን ድንበር ከ15-30 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ መሰማራቱን ያሳያሉ።

ዩክሬን በምስራቅ ያለውን ጦርነት ካላቆመች ለሚኖረው ደም መፋሰስ ተጠያቂ እንደምትሆን ፕሬዝዳንት ፑቲን አስጠንቅቀዋል። ቀደም ሲልም ተከታታይ የውሸት ክስተቶች የነበሩ ሲሆን አንዱን ምክንያት በመጠቀም ሩሲያ ጥቃት ልትሰነዝር ትችላለች።

ዩክሬን ወደ አውሮፓ ተቋማት ማለትም ወደ ኔቶ እና አውሮፓ ህብረት የምታደርገውን እርምጃ ሩሲያ ስትቃወም ቆይታለች። አሁን ደግሞ ዩክሬን የምዕራቡ ዓለም አሻንጉሊት እንደሆነች እና በማንኛውም ሁኔታ ትክክለኛ ሃገር እንዳልነበረች ፑቲን ገልጸዋል ።

ዋና ፍላጎታቸው ደግሞ ዩክሬን የ 30 ሃገሮች የመከላከያ ሃይል ጥምረት የሆነውን የሰሜን አትላንቲክ የጦር ቃል ኪዳን ድርጅት (ኔቶን) እንደማትቀላቀል ምዕራባውያን ዋስትና እንዲሰጡ ነው።