ትራምፕ 'ትሩዝ ሶሻል' የተባለ አዲስ ማኅበራዊ ሚዲያ ሊመሠርቱ ነው

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ 'ትሩዝ ሶሻል' የተባለ አዲስ ማኅበራዊ ሚዲያ ሊመሠርቱ መሆኑን አስታወቁ።
ትራምፕ ማኅበራዊ ሚዲያው በአሜሪካ የተቃዋሚ ድምጾችን ዝም በማሰኘት የሚታወቁ "ታላላቅ የቴክኖሎጂ ጭቆና ያስቆማል" ብለዋል።
ትራምፕ የሚመሩት ትራምፕ ሚዲያ እና ቴክኖሎጂ ቡድን (ቲኤምቲጂ) በደንበኝነት ምዝገባ ቪዲዮ-በፍላጎት የሚሰጥ አገልግሎት ለማስጀመር አስቧል።
በጥር ወር ደጋፊዎቻቸው የአሜሪካን ምክር ቤት ህንጻን ካፒቶል ሂልን በመውረራቸው ምክንያት ትራምፕ እንደ ትዊተር እና ፌስቡክ ካሉ ታዋቂ የማኅበራዊ ሚዲያ ትስስር መድረኮች በጊዜያዊነት ወይም በቋሚነት ታግደዋል።
እሳቸው እና አማካሪዎቻቸው ከዚያ በኋላ ተፎካካሪ የማኅበራዊ ሚዲያ ለመፍጠር ስለማቀዳቸው ፍንጭ ሰጥተዋል።
በዚህ ዓመት መጀመሪያ ላይ 'ከዶናልድ ጄ ትራምፕ ዴስክ' የሚባል ድረ-ገጽ ጀምረው ነበር።
ድረ-ገጹ ከተጀመረ ከአንድ ወር ባነሰ ጊዜ ውስጥ እስከወዲያኛው ተዘግቷል።
በቲኤምቲጂ መግለጫ መሠረት 'ትሩዝ ሶሻል' በሚቀጥለው ወር ለተመረጡ ሰዎች ብቻ ክፍት ሆኖ በአውሮፓውያኑ 2022 የመጀመሪያዎቹ ሦስት ወራት ደግሞ በአገር አቀፍ ደረጃ ይለቀቃል ተብሏል።
ትራምፕ "ታሊባን በትዊተር ላይ ትልቅ ቦታ ኖሮት ተወዳጁ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዝም እንዲል በተደረገበት ዓለም ውስጥ እየኖርን ነው" ሲሉ ጽፈዋል።
"ሁሉም ሰው ለምን ትልልቅ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎችን አትገዳደሩም ብሎ ይጠይቀኛል? ደህና፣ በቅርቡ ይሆናለን!" በማለት አክለዋል።
አዲሱ ኩባንያ የሚሠራ ገጽ እንዳለው የሚጠቁም ነገር የለም።
ትራምፕ ትዊተር ወይም ፌስቡክን የሚገዳደር መድረክ መፍጠር ቢፈልጉም ያ ግን በቀላሉ የሚሳካ አይመስልም።
ቲኤምቲጂ በፍላጎት መሠረት የሚሠራው የቪዲዮ አገልግሎት የመዝናኛ ፕሮግራምን፣ ዜናዎችን፣ ፖድካስቶችን እና ሌሎችንም ያሳያል ተብሏል።
ኩባንያው በናስዳክ የአክሲዮን ላይ ከተዘረዘረው ከስፔክ ጋር ለመዋሃድ አስቧል።
ትራምፕ አዲስ ማኅበራዊ ሚዲያ ይፋ የተደረገው የቀድሞው ረዳታቸው ጄሰን ሚለር 'ጌትር' የተባለ ሌላ የማኅበራዊ ሚዲያ ከጀመረ ከወራት በኋላ ነው።












