ሕዳሴ ግድብ፡ አል ሲሲ ግብጽ የምታገኘው ውሃ ከቀነሰ 'የከፋ አካባቢያዊ ቀውስ' ይከሰታል አሉ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ኢትዮጵያ እየገነባችው ባለው ግድብ ሳቢያ አገራቸው በምታገኘው የውሃ መጠን ላይ ተጽእኖ የሚፈጠር ከሆነ 'የከፋ አካባቢያዊ ችግር' ይፈጠራል ሲሉ የግብጹ ፕሬዝደንት አብዱል ፋታህ አል ሲሲ አስጠነቀቁ።
"አሁንም ደግሜ እንደምለው ማንም ከግብጽ ውሃ ላይ አንዲት ጠብታ መውሰድ አይችልም፤ ይህ ከሆነ ደግሞ ከሚታሰበው በላይ አደገኛ አለመረጋጋት በአካባቢው ይፈጠራል ሲሉ ተናግረዋል።
ፕሬዝደንቱ ጨምረውም "ማንንም እያስፈራራሁ አይደለም፤ ሁልጊዜም ንግግራችን ምክንያታዊና ሚዛናዊ ነው" ብለዋል።
ፕሬዝዳንቱ ይህንን የተናገሩት ዛሬ ማክሰኞ ተዘግቶ በሰነበተው የሱዊዝ መተላለፊያ ቦይ ላይ በተገኙበት ጊዜ ሲሆን አገራቸው ከኢትዮጵያና ከሱዳን ጋር የምታደርገው ድርድር እንዲቀጥል ፍላጎት እንዳላት ተናግረዋል።
በአምስት ቢሊዮን ዶላር ወጪ ኢትዮጵያ ባለፉት አስር ዓመታት ስትገነባው የቆየችው የታላቁ ሕዳሴ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ግድብ ግንባታው ወደ ሰማኒያ በመቶ መድረሱ ተነግሯል።
በግድቡ ዙሪያ ከስምምነት ላይ ለመድረስ ኢትዮጵያ፣ ሱዳንና ግብጽ ከግድቡ ግንባታ መጀመር አንስቶ ድርድር ቢያደርጉም መቋጫ ላይ ሳይደርሱ እስካሁን ቆይተዋል።
ኢትዮጵያ ባለፈው ዓመት ክረምት ወር ላይ የግድቡን የመጀመሪያ ደረጃ የውሃ ሙሌት ማከናወኗን ያሳወቀች ሲሆን በዚህ ዓመትም ሁለተኛውን ዙር የውሃ ሙሌት እንደምታካሄድ ገልጻለች።
አሁንም ሆነ ቀደም ሲል ኢትዮጵያ ከስምምነት ላይ ሳይደረስ ግድቡን በውሃ እንዳትሞላ ሱዳንና ግብጽ በተደጋጋሚ ቢወተውቱም ኢትዮጵያ ድርድሩ እየተካሄደ የውሃ ሙሌቱን አካሂዳለሁ በማለት አቋሟን ግልጽ አድርጋለች።
ሲቋረጥና ሲቀጥል የነበረው የሦስቱ አገራት ድርድር የተለያዩ አገራት በአሸማጋይነት የተሳተፉበት ሲሆን አሁን በዋናነት ጉዳዩን የአፍሪካ ሕብረት ይዞት ይገኛል።
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ሱዳንና ግብጽ ዓለም አቀፍ አደራዳሪዎች በሂደቱ ውስጥ ይሳተፉ የሚል ጥያቄ አቅርበው ውይይቱ የተቋረጠ ሲሆን ኢትዮጵያ ጉዳዩ የሦስቱ አገራትና የአፍሪካ ሕብረት በመሆኑ ሌላ ተጨማሪ አካል መሳተፉ አስፈላጊ አይደለም በማለት ሳትቀበለው ቀርታለች።
ሱዳንና ግብጽ በተደጋጋሚ ኢትዮጵያ ግድቡን ለሁለተኛ ጊዜ ውሃ እንዲይዝ ከማድረጓ በፊት አሳሪ ሕጋዊ ስምምነት መፈረም እንዳለበት ቢጠይቁም ተቀባይነት አላገኘም።
ኢትዮጵያ ግድቡን የምትጠቀመው ውሃውን በግዛቷ ውስጥ ለሚያስቀሩ ፕሮጀክቶች እንዳልሆነ በተደጋጋሚ ብታስረዳም ሱዳን በተለይም ግብጽ የትኛውም አይነት በውሃው ላይ የሚከናወን ሥራ የእነሱን ይሁንታ ሳያገኝ መካሄድ እንደሌለበት ሲገልጹ ቆይተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በቅርቡ በአገሪቱ ምክር ቤት ላይ ባደረጉት ንግግር "ውሃ አሞላሉን በተመለከተ ተደራድረን ስናበቃ እንሙላ ካልን ክረምቱ ያልፍና በዓመት 1 ቢሊየን ዶላር እናጣለን" ሲሉ የውሃ ሙሌቱን ማዘግየት እንደማይቻል አመልክተዋል።
የውሃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስትር የሆኑት ስለሺ በቀለም (ዶ/ር፣ ኢንጂ.) ኢትዮጵያ ወደ መጠናቀቁ የተቃረበውን የህዳሴ ግድብ ሁለተኛ ዙር የውሃ ሙሌት በምንም ዓይነት መልኩ እንደማታራዝመውና ለዚህም የሚያበቃ አሰራርና ምክንያትም እንደሌለ ተናግረዋል።
የዛሬ አስር ዓመት ኢትዮጵያ በራሷ ወጪ መገንባት የጀመረችው ታላቁ ህዳሴ ግድብ በአፍሪካ ትልቁ ሲሆን፣ ከአምስት ሺህ ሜጋ ዋት በላይ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጨት የሚችል አቅም ያለው ግዙፍ ግድብ ነው።
የግድቡ ግንባታ ይጠናቀቃል ከተባለበት ጊዜ በተለያዩ ምክንያቶች ለዓመታት የተጓተተ ሲሆን በአሁኑ ወቅት ግንባታው ከ79 በመቶ በላይ ደርሷል።
በሚጥለው ዓመትም በተወሰነ ደረጃ ኃይል የማመንጨት ሥራውን እንደሚጀምር ይጠበቃል።
ለአብዛኛው ሕዝቧና ለተለያዩ ኢንደስትሪዎቿ የሚሆን በቂ የኤሌክትሪክ ኃይል የማታመነጨው ኢትዮጵያ የህዳሴው ግድብ መጠናቀቅ በሕዝቧ ኑሮና በኢኮኖሚዋ ላይ ጉልህ ለውጥን እንደሚያመጣ በማሰብ የግድቡን ግንባታ እያካሄደች ትገኛለች።
የታላቁ ህዳሴ ግድብ ተጠናቅቆ ሥራውን ሲጀምር አስካሁን የኤሌትሪክ ኃይል ያላገኘው ከግማሽ በላይ የአገሪቱ ሕዝብ ብርሃን እንዲያገኝ ያስችለዋል ሲሉ የኢትዮጵያ ባለስልጣናት ሲገልጹ ቆይተዋል።














