ትግራይ ፡ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ልጅ ሰምሃል መለቀቋን እናቷ አዜብ መስፍን ገለጹ

የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ልጅ ሰምሃል መለስ ትግራይ ውስጥ በጸጥታ ኃይሎች ቁጥጥር ስር ከቆየች በኋላ መለቀቋን እናቷ ወይዘሮ አዜብ መሰፍን ለቢቢሲ ገለጹ።

ወ/ሮ አዜብ እንዳሉት ሰምሃል ከእሁድ ጀምሮ አስከ ሰኞ ምሽት ድረስ ለ36 ሰዓታት ተይዛ መቆየቷን ገልጸው፤ ትናንት ምሽት እራሷ ደውላ መለቀቋን እንደገለጸችላቸው ለቢቢሲ ዛሬ [ማክሰኞ] ጠዋት ተናግረዋል።

ወ/ሮ አዜብ ልጃቸው ሰምሃል በምን ምክንያት ለእስር እንደተዳረገች የሚያውቁት ነገር እንደሌለ ለቢቢሲ ተናገረው፣ ወደ መቀለ የሄደችው ወታደራዊ ግጭቱ ከመጀመሩ በፊት እንደሆነ ገልጸዋል።

አዲስ አበባ የሚገኙት ወ/ሮ አዜብ ጨምረውም ሰምሃል ወደ መቀለ ያቀናችው በአባቷ የህይወት ታሪክ ላይ የተጻፈ መጽሐፍን ተንተርሶ የተዘጋጀን ቲያትር ለማስመረቅ በርካታ ሰዎች ካሉበት ቡድን ጋር መሆኑን አመልክተዋል።

ሰምሃል "የፖለቲካ አቋም ሊኖራት ይችላል። ነገር ግን የፖለቲካ ፓርቲ አመራርም፣ አባልም፣ ደጋፊም አልነበረችም" ያሉት እናቷ ወ/ሮ አዜብ መስፍን የእስሯ ምክንያት ምን እንደሆነ እንደማያውቁ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

ከሰምሃል በተጨማሪ ከሁለት አስርት ዓመታት በፊት አዲስ አበባ ውስጥ የተገደሉት ጀነራል ኃየሎም አርአያ ልጅ የሆነው ብርሐነመስቀል ኃየሎምም በቁጥጥር ስር መዋሉ ተገልጿል።

ወ/ሮ አዜብ ከቀናት በፊት ልጃቸው ሰምሃል እየተፈለገች እንደሆነ በመስማታቸው አርብ ዕለት ወደ መቀለ ለመሄድ ፈልገው የነበረ ቢሆንም ፈቃድ ባለማግኘታቸው እንደቀሩና እሁድ ዕለት በቁጥጥር ሰር እንደዋለች መስማታቸውን ለቢቢሲ አብራርተዋል።

ሰምሃል በየትኛው አካል እንደተያዘችና ምክንያቱ ምን እንደሆነ ከአንዳንድ አካላት ለማወቅ ጥረት ማድረጋቸውን የሚናገሩት ወ/ሮ አዜብ ነገር ግን ምላሽ ለማግኘት እንዳልቻሉ ጠቅሰዋል።

ቢቢሲ ሰምሃል መለስ በቁጥጥር ስር ስለዋለችበት ምክንያትና ለማወቅ ከጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ፕሬስ ሴክሬታሪያት አወል ሱልጣን እና የፌደራል ፖሊስ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ጄይላን አብዲን ቢጠይቅም ስለጉዳዩ የሚያውቁት ነገር እንደሌለ ተናግረዋል።

ሰምሃል መለስ የኢህአዴግ ሊቀ መንበርና ከ20 ዓመታት በላይ አገሪቱን የመሩት የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ እና የወይዘሮ አዜብ መስፍን የበኩር ልጅ ስትሆን አስከ አባቷ ህልፈት ድረስ ስለእርሷ ብዙም የሚታወቅ ነገር አልነበረም።

የ32 ዓመቷ ወጣት ሰምሃል የተወለደችው አባቷ በኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማሪያም የሚመራውን መንግሥት ለመጣል ህወሓትን በመምራት የሽምቅ ውጊያ በሚያደርጉበት ጊዜ ሱዳን ካርቱም ውስጥ ነበር።

ሰምሃል ከአባቷ ህልፈት በኋላ የቀድሞውን ጠቅላይ ሚኒስትር ለመዘከር በሚካሄዱ እንቅስቃሴዎችና በፖለቲካዊ መድረኮች ላይ አልፎ አልፎ በመቅረብ ሃሰብ ስትሰነዝር ከመታየት ውጪ በፖለቲካው መድረክ ጎልቶ የታየ ተሳትፎ አልነበራትም።

ጥቅምት 24/2013 ዓ.ም በትግራይ ክልል ውስጥ በሚገኘው የአገሪቱ የመከላከያ ሠራዊት የሠሜን ዕዝ ላይ ጥቃት ከተፈጸመ በኋላ መንግሥት በህወሓት ኃይሎች ላይ ወታደራዊ ዘመቻ አካሂዶ የህወሓት አመራሮችን ከክልሉ የስልጣን መንበር ላይ ማስወገዱ ይታወሳል።

በትግራይ ክልል ውስጥ ለሦስት ሳምንታት ያህል ከተካሄደ ወታደራዊ ዘመቻ በኋላ ኅዳር 19/2013 ዓ.ም የፌደራል መከላከያ ሠራዊት የክልሉን ዋና ከተማ መቀለን ተቆጣጥሮ ይፈለጋሉ ያላቸውን ከፍተኛ የህወሓት አመራሮችን ለመያዝ ክትትል እያደረገ መሆኑን ገልጿል።