ትግራይ ፡ በመቀለ ከተማ ሦስት ወጣቶች ሞተው ተገኙ

የፎቶው ባለመብት, G/MEDHIN G/HER
በመቀለ ከተማ በአይደር ክፍለ ከተማ አዲሓ ተብሎ በሚታወቀው ሰፈር አንዲት ሴትና ሁለት ወንድ ጓደኛሞች በአንድ ቤት ውስጥ ሞተው ተገኙ።
ወጣቶቹ ሞተው የተገኙት በአንድ መኖሪያ ቤት ውስጥ መሆኑን በከተማዋ የሚገኘው የአይደር ክፍለ ከተማ ፖሊስ ለቢቢሲ ገልጿል።
ህይወታቸው አልፎ የተገኙት ሦስቱ ወጣቶች ርዕሶም ገብረእግዚአብሔር፣ ግርማይ ኃብተሚካኤል እና መርሃዊት ሐድጉ የተባሉት ጓደኛሞች መሆናቸው የተገለጸ ሲሆን እድሜያቸው ደግሞ በ20ዎች ውስጥ እንደሆነ ተነግሯል።
ሦስቱም ወጣቶች ባለፈው ቅዳሜ መስከረም ሁለት ቀን በጋራ ሲጫወቱ አምሽተው ወደ ቤታቸው እንደገቡ የተገለጸ ሲሆን፤ በማግስቱ እሁድ ከሰዓት ግን በአንደኛው ሟች ቤት ውስጥ ሞተው መገኘታቸው ታውቋል።
በአይደር ክፍለ ከተማ የወንጀል ምርመራ ክፍል ባልደረባ የሆኑት ምክትል ኢንስፔክተር ገብረማርያም የማነ እንዳሉት የወጣቶቹ ሞት መንስዔ ለማወቅ ፖሊስ መርመራ እያካሄደ እንደሆነ ለቢቢሲ ገልጸዋል።
ጨምረውም እስካሁን ባገኘው መረጃ ፖሊስ ለወጣቶቹ ሞት መንስዔ ተብሎ የሚጠረጠር ፍንጭ ያገኘ ቢሆንም፤ በአይደር ሆስፒታል የአስከሬን ምርመራ ተደርጎ ውጤት እስኪመጣለት ድረስ እየጠበቀ መሆኑንም መርማሪው ጨምረው ተናግረዋል።
የሟች ርዕሶም ገብረእግዚአብሔር ወንድም የሆነው ገብረ መድኅን ገብረእግዚአብሔር ለቢቢሲ እንደተናገረው ወጣቶቹ ተኝተውበት በነበረው ክፍል ውስጥ የነበረው ጄነሬተር ለሞታቸው መንስኤ ሊሆን እንደሚችል አመልክቷል።
ገብረመድኅን እንደሚለው ከሆነ ቅዳሜ ዕለት ወጣቶቹ በሚኖሩበት አካባቢ መብራት ጠፍቶ ስለነበር ጄኔሬተሩ አገልግሎት ሲሰጥ የነበረ ቢሆንም ማታ ግን ተለኩሶ ስለመቆየቱ መረጃ እንደሌለው ተናግሯል።
ህይወታቸው አልፎ የተገኙት ሦስቱ ወጣቶች አስከሬን ወደ አይደር ሆስፒታል ሲወሰዱ ከህልፈታቸው በፊት ከአፋቸው አረፋ ይደፍቁ እንደነበርም ጨምሮ ተናግሯል።
የጆስቱ ወጣቶች ድንገተኛ ሞት ዜና በርካታ የመቀለ ከተማ ነዋሪዎችን ያስደነገጠ ሲሆን፤ ለሞታቸው ሰበብ የሆነውን ምክንያት ለማወቅ የህክምናና የፖሊስ የመርመራ ውጤት እየተጠበቀ ነው።
















