ደቡብ ኮርያ፡ የዩቲዮብ ክብረ ወሰንን የሰባበሩት የኮርያ ድምጻውያን

የኮርያ የወንዶች ሙዚቃ ቡድን፣ ቢቲኤስ፣ በዩቲዩብ ታሪክ አዲስ ክብረወሰን ያስመዘገበ የሙዚቃ ቪዲዮ ለቋል። ሙዚቀኞቹ የዩናይትድ ኪንግደም የነጠላ ዜማ ሰንጠረዥንም ተቆጣጥረውታል።

ቢቲኤሶች የለቀቁት የሙዚቃ ቪዲዮ "ዳይናማይት" የሚሰኝ ሲሆን የዩቲዩብ ክብረወሰንን ብቻ ሳይሆን በዩናይትድ ኪንግደም ነጠላ ሙዚቃዎች ሰንጠረዥ ላይም አርብ ዕለት በአንደኝነት ተቀምጧል።

የቡድኑ የሙዚቃ ቪዲዩ አርብ ዕለት ብቻ በ24 ሰዓት ውስጥ 101.1 ሚሊዮን ጊዜ ታይቷል።

ከዚህ ቀደም 'ብላክ ፒንክ' የተሰኙ የኮሪያ የሙዚቃ ቡድን አባላት 'ሃው ዩ ላይክ ዛት' በሚለው የሙዚቃ ቪዲዮዋቸው 86.3 ሚሊዮን ተመልካቾችን በ24 ሰዓት ውስጥ በማግኘት የክብረወሰኑ ባለቤት ሆነው ነበር።

ይህንን ክብረ ወሰን እንደ ቀልድ ያለፉት ቢቲኤሶች በአንድ ቀን 100 ሚሊዮን ተመልካቾችን ማግኘት ችለዋል።

የሙዚቃ ክሊፑ በቀጥታ ሲሰራጭ ሦስት ሚሊዮን አድናቂዎቻቸው የተከታተሉት ሲሆን፣ ከዚህ ቀደም በብላክ ፒንኮች 'ሃው ዩ ላይክ ዛት' ተይዞ የነበረውን ክብረ ወሰን በእጥፍ በልጠዋል።

ቢቲኤሶች እንግሊዘኛን ከኮርያኛ ቀላቅለው በመዝፈን ይታወቁ የነበረ ቢሆንም 'ዳይናማይት' ግን ሙሉ በሙሉ በእንግሊዘኛ ያቀነቀኑት የመጀመሪያ ሥራቸው ነው።

ቡድኖቹ በጎ ሃሳብን፣ ተስፋን፣ ፍቅርን እና ንጹህ መንፈስን በሙዚቃቸው መስበክ እንደሚፈልጉ ገልፀዋል።

ቡድኑ ይህንን የሙዚቃ ቪዲዮ መልቀቅ የፈለጉት አድናቂዎቻቸውን በፍጥነት መድረስ በመፈለጋቸው መሆኑን ተናግረዋል። በኮቪድ-19 ምክንያት የዓለም ሕዝብ በበርካታ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ አልፏል ያሉት ቡድኑ አባላት ከአድናቂዎቻቸው ጋር በጎ ኃሳብን መጋራት እቅዳቸው ነው።

ሙዚቃው በ104 አገሮች አይቲዩንስ ላይ ከፍተኛ አድማጭ አግኝቷል።

ቢቲኤሶች ተቀናቃኝ አላጣቸውም፤ በአገራቸው ልጆች የተመሰረተው 'ብላክ ፒንክ' የተሰኘው ሙዚቃ ቡድን አርብ እለት የያዙትን የዩቲዩብ ክብረወሰን ለመስበር በመዛት ከሴሌና ጎሜዝ ጋር ጥምረት ፈጥረው የሰሩትን 'አይስ ክሬም' የተሰኘ የሙዚቃ ክሊፕ እንደሚለቅቁ ተናግረዋል።