በምስራቃዊ ቱርክ በተከሰተ የመሬት መንቀጥቀጥ ቢያንስ 18 ሰዎች ሞቱ

በምስራቃዊ ቱርክ በደረሰ ከፍተኛ ርዕደ መሬት ቢያንስ 18 ሰዎች ሲሞቱ በመቶዎች የሚቆጠሩት ለጉዳት መዳረጋቸውን ባለሥልጣናት አስታወቁ።

ትናንት ምሽት 3 ሰዓት ገደማ የተከሰተው ርዕደ መሬት በሬክተር ስኬል 6.8 ማግኒዩቲዩድ ተለክቷል።

ርዕደ መሬቱ ኢላዚግ ግዛት ሲቭራይስ ከተማን በዋናነት የመታ ሲሆን በከተማዋ ለበርካታ ሕንፃዎች መፈራረስ እና ነዋሪዎች ወደ መንገዶች እንዲሸሹ ምክንያት ሆኗል።

የቲግሪስ ወንዝ መነሻ በሆነው በሃዛር ሐይቅ ዳርቻ የምትገኘው እና 4 ሺህ የሚጠጉ ሰዎች የሚኖሩባት ከተማ -ሲቭራይስ የጎብኝዎች መዳራሻ ናት።

ርዕደ መሬቱ በጎረቤት አገር ሶሪያ፣ ሊባኖስ እና ኢራንም ተሰምቷል።

በቱርክ ርዕደ መሬት ማጋጠሙ የተለመደ ነው። በአውሮፓዊያን 1999 በምዕራባዊቷ ከተማ ኢዝሚት በደረሰ ከፍተኛ ርዕደ መሬት 17 ሺህ ሰዎች ሕይወታቸው አልፏል።

እንደ ቱርክ ድንገተኛ አደጋዎች መቆጣጠር ባለሥልጣን ከሆነ ርዕደ መሬቱ ከተከሰተ በኋላ 60 ጊዜ ቀላል የመሬት መንቀጥቀጥ አጋጥሞ ነበር።

ባለሥልጣናቱ እንዳሉት ከ400 የሚበልጡ የነፍስ አድን ሠራተኞች በአደጋው ምክንያት ለተፈናቀሉ ሰዎች አልጋ እና ድንኳን ይዘው ወደ አካባቢው እያመሩ ነው።

ምን አልባት ከከባድ ርዕደ መሬቱ በኋላ ሌሎች አነስተኛ የመሬት መንቀጥቀጥ ሊኖር ስለሚችል ሰዎች ወደ ፈራረሱት ሕንፃዎች ተመልሰው እንዳይሄዱም ባለሥልጣኑ አስጠንቅቋል።

የአላዚግ አስተዳዳር በግዛቷ ስምንት ሰዎች መሞታቸውን የገለፀ ሲሆን የጎረቤት ማላትያ ግዛት አስተዳዳር ደግሞ ስድስት ሰዎች መሞታቸውን አስታውቋል።

"በጣም የሚያስፈራ ነበር፤ የቤት ውስጥ እቃዎች እኛ ላይ ወደቁ፤ ከዚያም ተሯሩጠን ወደ ውጭ ወጣን" ሲል በኢላዚግ ነዋሪ የሆኑትን ምላሃት ካንን ጠቅሶ ኤ ኤፍ ፒ የዜና ወኪል ዘግቧል።