ጃፓን ያለ መሬትና ያለ አርሶ አደሮች የፈጠረችው የግብርና አብዮት

ከመቶ አመት በፊት እንዲያውም ብዙ ሳንርቅ ኧረ ከሃያ አመታት በፊት ያለ መሬትና አርሶ አደሮች ግብርናን ማካሄድ ይቻላል ብሎ ማሰብ ሩቅ ህልም ነበር።

በጃፓን ግን እውን ሆኗል። በጃፓን ነዋሪ የሆነው ዩቺ ሞሪ ፍራፍሬዎችንና አትክልቶችን ቢያበቅልም፤ መሬትም ሆነ አፈር ለሱ አስፈላጊ አይደለም።

በአማራጩ የጃፓን ሳይንቲስቶች የሰውን ልጅ ኩላሊት ለማከም የተሰራውን በግልፅ የሚያሳይና ፈሳሽም ሆነ አየር ማሳለፍ የሚችል 'ፖሊመር ፊልም' የተባለውን ፕላስቲክ መሳይ ነገር ለግብርና መጠቀም ከጀማመሩ ሰነባበቱ።

አዝርዕቱ 'ፖሊመር ፊልሙ' ላይ የሚበቅሉ ሲሆን ፈሳሽም ሆነ ንጥረ ነገሮችን ለማጠራቀምም ይረዳል።

አትክልቶችን የትኛውም ከባቢ እንዲበቅሉ ከማስቻል በተጨማሪ ከባህላዊው ግብርና 90 ፐርሰንት ያነሰን ውሃን በመጠቀም ፀረ ተባይ መድሃኒቶችንም ከጥቅም ውጭ አድርጓቸዋል። ምክንያቱም ፖሊመሩ ቫይረስንም ሆነ ባክቴሪያን ማገድ ስለሚያስችለው ነው።

በጥቂት የሰው ኃይልና ያለምንም መሬት የግብርናን አብዮት የፈጠረችበት አንዱ መንገድ ነው።

"በኩላሊት እጥበት (ዲያሊሲስ) ወቅት ደምን ለማጣራት የሚጠቅመውን እቃ በመውሰድ ነው መጠቀም የጀመርኩት" በማለት ሳይንቲስቱ ዩይቺ ሞሪ ለቢቢሲ ተናግሯል።

ኩባንያው ሜቢኦል ይሄንን ፈጠራውን በ120 ሃገራት ማስመዝገብ ችሏል።

በጃፓን እየተካሄደ ባለው የግብርና አብዮት የእርሻ መሬቶች ወደ ቴክኖሎጂ ማዕከላት እየተቀየሩ ሲሆን ለዚህም አርቲፊሻል ኢንተለጀንስና የመጠቁ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ተግባራዊ በመሆን ላይ ናቸው።

የዚህ አመት የተባበሩት መንግሥታት የውሃ ሃብትና ልማትን በተመለከተ ባወጣው ሪፖርቱ ያለው የከባቢ መሸርሸርና የውሃ ሃብት መመናመን በዚህ ከቀጠለ በ2050 40 % የሚሆነው የአዝርዕት ምርቶችና 45% የሚሆነው የአለም ምርት ቀውስ ውስጥ እንደሚወድቅ ነው።

ዩቺ ሞሪ የፈጠረው የአበቃቀል ዘዴ በጃፓን ከ150 በላይ ቦታዎች ተግባራዊ ሲሆን በተባበሩት አረብ ኤምሬትስ አገራትም ተጠቃሚ ሆነዋል።

በተለይም ይህ ዘዴ በጎርጎሮሳውያኑ 2011 የተፈጠረውን የኒውክለር ቀውስ ተከትሎ በተፈጠረው የመሬት መንቀጥቀጥ ምክንያት ጨረሮች ባስከተሉት የእርሻ መሬቶችን ብክለትን ለማስተካከልም ይረዳሉ ተብሏል።

ሮቦት ትራክተሮች

በ2050 የአለም አቀፉ የህዝብ ቁጥር ከ7.7 ቢሊዮን ወደ 9.8 ቢሊዮን ያድጋል ተብሎ እየተገመተ ባለበት ወቅት፤ የተለያዩ ኩባንያዎች ሊመጣ የሚችለውን የምግብ ፍላጎትን ለሟሟላት የተለያዩ የቢዝነስ አማራጮችን በመፈተሽ ላይ ናቸው።

የጃፓን መንግሥት በአሁኑ ሰዓት በግብርና ስራዎች ከመዝራት እስከ ማረም ባለው ሂደት ላይ ሊያግዙ የሚችሉ 20 አይነት ሮቦቶች መመረት ላይ ከፍተኛ እርዳታ እያደረገ ነው።

ከሆካይዶ ዩኒቨርስቲ ጋር በመጣመር ያንመር የተባለው አምራች ድርጅት አንድ ሮቦት አምርቶ በእርሻ መሬቶች ላይ እየተሞከረ ነው።

መሬት ላይ ያሉ ቁሶችን ለመለየትም የሚያስችል መሳሪያ ስለተገጠማላቸው አንድ ሰው ሁለት ትራክተሮችን በተመሳሳይ ሰዓት ላይ ሊያሰራቸው ይችላል።

በዚህ አመትም ኒሳን በፀሐይ ጉልበት የሚሰሩ፣ አቅጣጫን የሚያመላክቱና የዋይፋይ አገልግሎት የተገጠመላቸው ሮቦት አምርቷል።

ዳክየ (ደክ) የሚል ስያሜ የተሰጠውና ሳጥን የሚመስለው ሮቦት በሩዝ እርሻዎች ውስጥ በመመላለስ ውሃው ውስጥ ያለውን የኦክስጅን መጠን በመጨመር፣ የፀረተባይ መድሃኒቶችን መጠን መቀነስ አስችሏል።

እርሻ በጥቂት ሰዎች

በቴክኖሎጂ በመታገዝ የእርሻ መሬት ላይ በቀጥታ መስራት የማይፈልጉና በቴክኖሎጂውም ብዙ ዕውቀት የሌላቸው ወጣቶችን ለመሳብ የጃፓን መንግሥት አቅዷል።

በጥቂት የሰው ኃይልም የግብርና ዘርፉንና የምጣኔ ኃብቱን ለማሳደግ ይረዳልም ተብሏል።

በባለፉት አስር አመታት በግብርና ዘርፍ የተሰማራው የሰው ኃይል ከ2.2ሚሊዮን ወደ 1.7 ሚሊዮን አሽቆልቁሏል።

ከዚህ በከፋ ሁኔታም በግብርና ስራ ላይ የተሰማሩት ሰዎች አማካኝ እድሜ 67 አመት ሲሆን፤ ብዙ አርሶ አደሮችም በትርፍ ጊዜያቸው ነው የሚሰሩት።

ሌላኛው የጃፓንን ግብርና የሚገድበው የሃገሪቷ መልክዓ ምድር አቀማመጥ ሲሆን በዚህም ምክንያት 40% የሚሆነውን የሃገሪቷን ምርት ብቻ ነው ማምረት የተቻለው።

85% የሚሆነው የሃገሪቷ የእርሻ ቦታ ተራራማ ሲሆን ቀሪው ደግሞ የሚያበቅለው ሩዝ ብቻ ነው።

ሩዝ የጃፓናውያን ዋነኛ ምግብ ሲሆን ለሩዝ አምራች ገበሬዎች የመንግሥታቸው ድጋፍ አልተለያቸውም።

በግብርና ላይ የሰው አልባ አውሮፕላኖች (ድሮኖች) ጥቅም

ምንም እንኳን ለዘመናት ሩዝ ዋነኛ ምግብ ሆኖ ቢቆይም የአበላል ባህል በመቀየሩ በጎርጎሳውያኑ አቆጣጠር 1962 በአማካኝ በአመት አንድ ሰው 118ኪ.ግ ሩዝ ተጠቃሚነት በ2006 ወደ 60ኪ.ግራም ቀንሷል። ይህንንም በማየት ጃፓን የተለያዩ አዝርዕቶችን የሚያመርቱ አርሶ አደሮችን እያበረታታች ነው።

የሰው እርዳታ ዝቅተኛ በመሆኑም አርሶ አደሮች ወደተለያዩ ማሽኖችና የቴክኖሎጂ ውጤቶች ፊታቸውን አዙረዋል።

በከፍተኛ ሁኔታም ሰው አልባ አውሮፕላኖች (ድሮኖች) ጥቅም ላይ እየዋሉ ሲሆን፤ አንድ ሰው ሙሉ ቀን የሚፈጅበትንም ስራ በግማሽ ሰዓት ውስጥ ማጠናቀቅ ችለዋል።

የተለያዩ ንጥረ ነገሮችን በመጠቀም ከመሬት ይልቅ ውሃ ውስጥ የሚያድጉ ፍራፍሬዎችንና አትክልቶችን ለማምረት ችለዋል።

ሚራይ የተባለው ቡድንም በመደርደሪያዎች ላይ በመትከል 10ሺ የሚሆኑ የሰላጣ ራሶችን በቀን ማብቀል ችለዋል።

በተገጠመለት መሳሪያ፤ የአርቲፊሻል ብርሃን፣ የእርጥበት መጠን፣ ካርቦንዳይኦክሳይና የሙቀትን መጠን ይቆጣጠራል።

አርቲፊሻል ብርሃን አትክልቶችን በከፍተኛ ፍጥነት ለማደግ የሚረዳቸው ሲሆን በበሽታ የመጠቃት እድላቸውንም ሙሉ በሙሉ ያጠፋዋል።

ምርታማነት በከፍተኛ ሁኔታ የጨመረ ሲሆን፤ በዚህም ምክንያት አትክልት የሚያመርቱ ፋብሪካዎች ቁጥር በሶስት እጥፍ አድጓል።

በውሃ ውስጥ የሚመረተው (ሃይድሮኒክስ) ከ1.5 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት ቢዝነስን የያዘ ሲሆን፤ በ2023 6.4 ቢሊዮን ይደርሳልም ተብሏል።

የቴክኖሎጂ ሸግግር

ጃፓን ከራሷ አልፋ፣ የአፍሪካ ሃገራት የሩዝ ምርታቸውን በማሳደግ በ2030፣ 50ሚሊዮን ቶን እንዲያመርቱ ለማስቻል ፕሮጀክቶችን ቀርፃለች።

በአንዳንድ ቦታዎችም ለምሳሌ በሴኔጋል ጃፓን በግብርና ላይ ለተሰማሩ ሰዎች ስልጠና ከመስጠት በተጨማሪ በመስኖ ስራ ላይም የቴክኖሎጂ ውጤቶችን እየተገበሩ ነው።

ይህንንም ተከትሎ በሄክታር አራት ቶን ይመረት የነበረውን ወደ ሰባት በማሳደግ የአምራቾቹም ገቢ በ20% እንዲጨምር ሆኗል።

በቪየትናም፣ በማይናማር፣ እንዲሁም በብራዚል ተመሳሳይ ፕሮጀክቶችን ቀርፃ እየሰራች ነው።

ከዚህ ሁሉ በላይ ግን የጃፓን አላማ ቴክኖሎጂን በመጠቀም የሀገሯን የምግብ ደህንነት ማረጋገጥ ነው።