ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ሴቶችን እያነቀ የገደለው ኮሪያዊ ከ30 ዓመታት በኋላ ተገኘ
የደቡብ ኮሪያ ፖሊስ ከሠላሳ ዓመታት በፊት በርካታ ሴቶችን የደፈረውና የገደለውን ኮሪያዊ እንዳገኘው አስታወቀ። ምርመራው ረዥም ጊዜ የፈጀ የወንጀል ምርመራ ተብሏል።
የደቡብ ኮሪያ ፖሊስ በደቡባዊ ሲዑል፤ በሀዋሴኦንግ ገጠራማ ክፍል የተገደሉ የ10 ሴቶችን ሞት ለማጣራት ከአውሮፓዊያኑ 1986 እስከ 1991 ባሉት ዓመታት 1.8 ሚሊየን የሥራ ቀናትን መድቦ ምርመራ ሲያካሂድ ቆይቷል።
አዲስ የተገኘው የዘረ መል ምርመራ ውጤት፤ የ56 ዓመቱ ተጠርጣሪ ሊ ቹንግ ጃኤ፤ በትንሹ በሦስቱ ሴች ግድያ እጁ እንዳለበት አመላክቷል።
ተጠርጣሪው ግለሰብ የወንድሙን ሚስት በመድፈርና በመግደል ወንጀል እንደ አውሮፓዊኑ በ1994 እድሜ ይፍታህ ተፈርዶበት ነበር።
ይሁን እንጅ ግለሰቡ ድርጊቱን እንዳልፈፀመ በማስረዳት ሊከሰስ እንደማይገባ ተቃውሞ አሰምቷል። የደንቡ ጊዜ በማለፉ ክስ እንደማይመሰረትበት ፖሊስ አስረድቷል።
ግድያዎቹ በአሥራዎቹ እድሜ ክልል ከሚገኙ ሴት ሕጻናት እስከ 70 ዓመት አዛውንት የደረሰ ነበር። ጉዳዩ ታዲያ ደቡብ ኮሪያዊው ፈልም ሠሪ ቦንግ ጆን የ2003ት ምርጥ ተሸላሚ የሆነው 'ሜሞሪስ ኦፍ መርደር' የሚል ፊልም እንዲሠራ ምክንያት ሆኖታል።
ተጠርጣሪውን ለማግኘት ፖሊስ 21 ሺህ ሰዎች ላይ ምርመራ ያካሄደ ሲሆን፤ ከ20 ሺህ በላይ ሰዎችን የጣት አሻራ ወስዶ ለማመሳከር ሞክሮ ነበር። ግን ፍንጭ ሳይገኝበት ቆይቷል።
"እስካሁን ድረስ ለዚህ ጉዳይ እልባት ሳንሰጥ ለረዥም ጊዜ በመቆየታችን ለሟቾችና ለሟች ቤተሰቦች እንዲሁም ለኮሪያ ሕዝብ የተሰማኝን ጥልቅ ሃዘን እገልፃለሁ" ሲሉ የግዮንጊ ናምቡ ግዛት የፖሊስ ኤጀንሲ ኃላፊ፤ ባን ጊ ሶ ለኤ ኤፍ ፒ የዜና ወኪል ተናግረዋል።
"ታሪካዊ የሆነ ኃላፊነት ስላለብን እውነቱን ለማውጣት የምንችለውን ሁሉ እናደርጋለን" ሲሉ አክለዋል።
እንደ የኮሪያው የዜና ምንጭ ዮን ሃብ ከሆነ ሴቶቹ የተገደሉት ታንቀው ነው። ግለሰቡ ለግድያው እንደ ካልሲ እና 'ስቶኪንግ' ያሉ የራሳቸውን አልባሳት ሳይጠቀም እንዳልቀረ ገልጿል።