ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
በሃየሎም ይምሉ የነበሩት ጄነራል ሰዓረ መኮንን ማን ናቸው?
ትናንት በተሰነዘረባቸው ድንገተኛ ጥቃት ህይወታቸውን ያጡት ጄነራል ሰዓረ መኮንን በልጅነታቸው ወደ ትግል ከተቀላቀሉ ጊዜ ጀምሮ ሙሉ ህይወታቸውን በወታደራዊ አገልግሎት ነበር ያሳለፉት።
በትግራይ ክልል ልዩ ስሙ ሽረ እንዳባጉና የተወለዱት ጄነራል ሰዓረ መኮነን፤ የመጀመርያ ደረጃ ትምህርታቸውን እዚያው ተከታትለዋል።
ሆኖም የሕዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ ከተመሰረተ ሁለት ዓመት ሳይሞላው በ1968 ዓ.ም ነበር በ17 ዓመታቸው ትምህርታቸውን አቋርጠው ትግሉን የተቀላቀሉት። እዚያም ከተራ ታጋይነት ተነስተው በተለያዩ ወታደራዊ አመራር እርከን ላይ አገልግለዋል።
በቀይ ኮከብ ዘመቻም ወደ ኤርትራ ለድጋፍ ከዘመተው የህወሓት ቡድን ጋር በአመራርነት ተጉዘው ለአንድ ዓመት ያህል እዚያው ቆይተዋል።
"ከደርግ ሠራዊት ጋር በተደረገው ጦርነት ሰዓረ ያልተሳተፈበት ውጊያ የለም" ማለት ይቻላል - ይላሉ ጀግነታቸውን የሚያውሱት የትግል ጓዶቻቸው።
በርካታ ታጋዮች በውሃ ጥም ያለቁበት ሰርዶ በተባለ የአፋር ክልል ውስጥ ከፍተኛ ተጋድሎ አድርገው በህይወት ከቀሩት ጥቂት ታጋዮች መካከል አንዱ ሲሆኑ፤ በጄነራል ሓየሎም የክፍለ ጦር ኣዛዥነት ስር ከፍተኛ አመራር ሆነው በዘመቻው ተሳታፊ ነበሩ።
በመጨረሻም በደብረ ታቦርና በሰሜን ሽዋ በተረደገው ከፍተኛ ውጊያ የብርጌድ አዛዥ በኋላም የክፍለ ጦር መሪ ሆነው ድል ማስመዝገባቸው የህይወት ታሪካቸው ያትታል።
ከደርግ ውድቀት በኋላ
ከደርግ ውድቀት በኋላ በተለይ በምሥራቅ ኢትዮጵያ ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዥ ሆነው የሰሩ ሲሆን፤ በኢትዮ ኤርትራ የድንበር ጦርነት ወቅት የቡሬ ግንባርን በመምራት የኢትዮጵያ ሠራዊት ከፍተኛ ድል እንዲቀዳጅ ካደረጉ የጦር ኣዛዦች መካከል ተጠቃሽ መሆናቸው ይነገራል።
ከጦርነቱ በኋላ በ2004 የአገር መከላለከያ ሠራዊት እንደ አዲስ ሲደራጅ፤ የሃገሪቱ ጦር ሠራዊት በሁለት ቦታዎች ተከፍሎ ሲዋቀር የአንዱን ዕዝ አዛዥ ሆነው ከፍተኛ አመራር ሰጥተዋል።
ቀጥሎም አደረጃጀቱ ተተሻሽሎ አኣራት ዕዞች ሲዋቀር፤ በተለይ የኢትዮ ኤርትራ ድንበር አካባቢ ተሰማርቶ የነበረው የሰሜን ዕዝ ዋና አዛዥ ሆነው ረዘም ላለ ጊዜ መርተውታል።
ከአራት ዓመት በፊት ግን ባልታወቀ ምክንያት ከዚሁ ኃላፊነታቸው ተነስተው የስልጠና ዋና መምርያ ከፍተኛ ኃላፊ ሆነው ሲሰሩ ነበር።
ባለፈው ዓመት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ ወደ ስልጣን ከመጡ በኋላ የመከላከያ ሠራዊቱ መልሶ ሲዋቀር በርካት የህወሓት ነባር ተጋዮች ከኃላፊነታቸው ሲነሱ ጄነራል ሰዓረ መኮንን ግን የቀድሞውን ኤታማዦር ሹም ጄነራለ ሳሞራ የኑስን ተክተው ህይወታቸው እስካለፈበት ቀን ድረስ ለአንድ ዓመት ሲሰሩ የጦር ኃይሉን መርተዋል።
"ሃየሎም ይሙት"
ጄነራል ሰዓረ መኮንን የጄነራል ሃየሎም አርአያ የትግል ጓድ ከመሆናቸውም ባሻገር የቅርብ ጓደኞች እንደነበሩ ይነገራል። የሶርዶውን ጨምሮ በተለያዩ የውጊያ ውሎዎች አንድ ላይ ተሳትፈው እንደነበሩ ይነገራል።
በነበራቸው ጥብቅ ግንኙነት የተነሳም ጄነራል ሃየሎም ከተገደሉ በኋላ "ሃሎም ይሙት" እያሉ ይምሉ እንደነበር በቅርብ የሚያውቋቸው ለቢቢሲ ተናግረዋል። ጨምረውም ጄነራል ሰዓረ በባህሪም ከጄነራል ሃየሎም ጋር በጣም እንደሚቀራረቡ ይመሰክራሉ።
ጄነራሉን በተለያዩ አጋጣሚዎች የሚያውቋቸው ሰዎች እንደሚመሰክሩት፤ በቀላሉ ከሰው ጋር መግባባት የሚችሉ፣ ተጫዋችና ርህሩህ እንደነበሩ ይመሰክራሉ።
ጄነራል ሰዓረ የሁለት ልጆች አባት ሲሆኑ የመጀመርያ ልጃቸው በትግል ላይ ሳሉ የተወለደች ሲሆን ሁለተኛው ልጃቸው ደግሞ ከደርግ መውደቅ በኋላ ነው የተወለደው።