በሰሜን ናይጄሪያ ጎሬላ 7 ሚሊየን ናይራ በላ ተባለ

የፎቶው ባለመብት, AFP
በሰሜን ናይጄሪያ ጎሬላው 7 ሚሊየን ናይራ (566222 ብር) ቅርጥፍ አድርጎ በላ ተባለ።
የካኖ የእንስሳት መኖሪያ የበላይ ኃላፊ ዑማር ካሼኮቦ ለቢቢሲ "ፖሊስ የተፈጠረውን እየመረመረ ነው፤ ማለት የምችለው ገንዘቡ ጠፍቷል ብቻ ነው" ብለዋል።
ገንዘቡ የተሰበሰበው ወደ እንስሳት ማቆያ ከሚከፈል መግቢያ ሲሆን የአምስት ቀን ገቢ እምጥ ይግባ ስምጥ አልታወቀም ሲሉ ተናግረዋል የካኖ ፖሊስ ቃል አቀባይ አብዱላሂ ኪያዋ።
እስካሁን ድረስ 10 ሰዎች በቁጥጥር ስር ውለው ይህን ያህል ገንዘብ እንዴት በካዝናችሁ አስቀመጣችሁ? ለምን ባንክ አላስገባችሁትም? ተብለው እየተመረመሩ ነው።
የገንዘቡን መጥፋት ለመጀመሪያ ጊዜ የዘገበው በካኖ አካባቢ የሚሠራጨው ፍሪደም ራድዮ ነበር።
በወቅቱ ለራድዮ ጣቢያው ቃለ-መጠይቅ የሰጡት የእንስሳት ማቆያው ፋይናንስ ባልደረባ ጎሬላው ወደ ገንዘብ ቤቱ ገብቶ ከሰረቀ በኋላ ዋጠው ሲሉ ተናግረዋል።
ባለፈው ዓመት በቤኑ ግዛት የናይጄሪያ ብሔራዊ ፈተና ድርጅት ባለሥልጣን ለፈተናና ተያያዥ ወጪዎች እርሳቸው ጋር የተቀመጠውን 36 ሚሊየን ናይራ (2911999 ብር) እባብ ወደ ቢሯቸው ገብቶ እንደዋጠው ተናግረው ነበር።
እኚህ ግለሰብና ሌሎች ባለሥልጣናት ላይ በማጭበርበር የተመሰረተባቸው ክስ ከጥቂት ሳምንታት በፊት ጥፋተኛ አይደሉም የሚል ውሳኔ አግኝቷል።
















