የበርካታ ዕፅዋት ከምድረ-ገፅ መጥፋት ለፍጡራን ሁላ አሳሳቢ ነው ተብሏል

የፎቶው ባለመብት, REBECCA CAIRN WICKS
ባለፉት 250 ዓመታት 600 ገደማ ዕፅዋት ከምድረ-ገፅ መጥፋታቸውን አንድ አዲስ ጥናት ይፋ አድርጓል።
ጥናቱ 600 ያክል ዕፅዋት ከምድረ ገፅ መጥፋታቸው ለፍጡራን እጅግ አሳሳቢ ነገር ነው ሲል ማስጠንቀቂያ አዘል መልዕክት ያስተላልፋል።
ቁጥሩ በተመሳሳይ ጊዜ ከምድረ-ገፅ ከጠፉ አእዋፍ፣ አጥቢ እንስሳት እና ውሃ ውስጥ የሚኖሩ እንስሳት እጥፍ እንደሆነ ነው ጥናቱ የሚያሳየው።
ሳይንቲስቶች ዕፅዋቱ እየጠፉ ያሉት በተፈጥሯዊ ሂደት መጥፋት ከነበረባቸው በ500 እጥፍ ፍጥነት መሆኑ አሳሳቢ ያደርገዋል ይላሉ።
ባፈለው ግንቦት የተባበሩት መንግሥታት አንድ ሚሊዮን ዕፅዋት እና እንስሳት ከምድረ-ገፅ ሊጠፉ ነውና እናስበበት ሲል መደመጡ አይዘነጋም።
ዶክተር አሊስ ሃምፍሬይስ «የእንስሳት ከዚህች ምድር መጥፋት ብዙም ላያስገርም ይችላል፤ የዕፅዋት ግን እጅጉን ሊያስጨንቀን የሚገባ ጉዳይ ነው» ይላሉ።
«ጥናታችን የትኞቹ ዕፅዋት የውሃ ሽታ ሆነው እንደቀሩ፤ እንዲሁም የጠፉበት ፍጥነት እንዴት አስደንጋጭ እንደሆነ ያሳያል» ይላሉ ዶክተሯ አክለው።
ከጠፉት ዕፅዋት መካከል ለወይራ ዘይት ምርት ጥቅም ላይ የሚውሉ የተወሰኑ እንደሚገኙበት ጥናቱ ይጠቁማል።
ባለፉት ሁለት ከግማሽ ምዕት ዓመታት ምድራችንን የተሰናበቱ ዕፅዋት ቁጥር 571 ሲሆን፤ 217 ደግሞ የአእዋፍ፣ የአጥቢ እና ውሃ ውስጥ የሚኖሩ እንስሳት ቁጥር ነው።
ምድር ላይ የሚኖሩ ፍጡራን [የሰው ልጅን ጨምሮ] የሚተነፍሱት ኦክስጅን ከዕፅዋት መሆኑ ጉዳዩን አሳሳቢ እንደሆን አድርጎታል።














