ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
በሁዋዌ ስልኮች ላይ በቅድምያ የሚጫኑ መተግበሪያዎችን እንዲቆሙ ተደረገ
ፌስቡክ መተግበሪያዎቹ በቅድምያ የሁዋዌ ስልኮች ላይ እንዳይጫኑ እርምጃዎችን መውሰዱን ሮይተርስ ዘገበ።
እገዳው የፌስቡክን ዋና መተግበሪያ የሚያካትት ቢሆንም በስሩ የሚተዳደሩትንም ዋትሳፕንና ኢንስታግራምንም ይጨምራል።
አሜሪካ፤ ከወራት በፊት የአሜሪካ ግዙፍ ኩባንያዎች ለደህንነት ሲባል ከሌሎች የቴሌኮም አገልግሎት አቅራቢዎች ጋር እንዳየይሰሩ ላቀረበችው ጥሪ የተወሰደ እርምጃ ነው።
የሁዋዌ የእጅ ስልክ ያሏቸው ሰዎች በቅድምያ ተጭነው የተሰጧቸውን መተግበሪያዎች እንደቀድሞው መጠቀም ይችላሉ።
ለእነርሱም ከፌስቡክ በየጊዜው መረጃዎች እንዲደርሳቸው እንደሚደረግም ተናግረዋል።
የፌስቡክን ውሳኔ ተከትሎ ከሁዋዌ የተሰጠ ምላሽ የለም።
ይህ ውሳኔ በእርግጥ በቅድምያ የተጫኑ መተግበሪያዎችን እንጂ የሁዋዌ ስልክ ያላቸውን ሰዎች መተግበሪያዎችን ማውረድም ሆነ መጠቀም አያግድም።
ወደፊት ግን ጉግል ከ'ፕሌይ ስቶር' ማለትም ከመተግበሪያ ማዕቀፍ የሁዋዌ ስልኮችን ቢያግድ ለሁዋዌ ስልክ ተጠቃሚዎች አስቸጋሪ ይሆናል።
ይህ ውሳኔ ለሁዋዌ በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንደማለት ነው።በዚሁ ሳምንት ነበር ከነሐሴ ጀምሮ የጉግልን አንድሮይድ ሶፍትዌር ከመጠቀም እንደታገደ የታወቀው።
አሁንም ግን በ'ፕሌይ ስቶር' ያሉ የጉግል መተግበሪያዎች በሙሉ የሁዋዌ የስልክ ቀፎዎች ላይ ይሰራሉ።
ሌሎች ሃገራትም በሁዋዌ መሣሪያዎች ላይ ገደቦች ብቻ ሳይሆን እገዳም እያደረጉ ነው።