በ500 መዥገሮች የተወረረው እባብ የደም ህዋስ ማነስ አጋጠመው

500 መዥገሮች ከሰውነቱ ላይ የተነሳለት እባብ የቀይ ደም ህዋሳት እጥረት አጋጥሞት የአውስትራሊያ የእንስሳት ሃኪሞች ህክምና እያደረጉለት ነው።

እባቡ ኢንፌክሽን አጋጥሞት እንቅስቃሴው ተገድቦ የነበረ ሲሆን፤ ይህም መዥገሮች በቀላሉ እንዲይዙት እድል ፈጥሮላቸውል ብሏል ከረምቢን የተሰኘ የዱር እንስሳት ሆስፒታል።

መዥገሮች ደም በመምጠጥ ቀይ የደም ህዋስ እጥረትን ያስከትላሉ። እባቡ የገጠመውም ይህ ነበር።

የእንስሳቱ የህክምና ተቋም እንዳስታወቀው፤ ከወራት በኋላ እባቡ ሲያገግም ተመልሶ ወደ መኖሪያ ስፍራው ይለቀቃል።

ከዚህ ቀደም ተመሳሳይ ችግር አጋጥሞት ለነበረ 'ኮአላ' ለተሰኘ እንስሳ ተመሳሳይ ህክምና ተደርጎ ነበረ።

'ኮአላ' የአውስትራሊያ ብርቅዬ እንስሳ ሲሆን፤ በመዥገር ተወሮ ወደ ህክምና ተቋሙ ከተወሰደ በኋላ አስፈላጊውን ህክምና ተደርጎለት ወደ ዱር ተመልሷል።

የእንስሳት ሃኪሞች እንደሚሉት፤ የዱር እንስሳት ከሌሎች እንስሳት በተሻለ በመዥገርና በሌሎች ፓራሳይቶች የመያዝ እድላቸው ዝቅተኛ ነው።

ሆኖም እንስሳቱ በበሽታ ከተጠቁና እንቅስቃሴያቸው ከተገደበ በቀላሉ በመዥገር ሊያዙ ይችላሉ። መዥገሮቹም በፍጥነት ቁጥራቸውን በመጨመር የእንስሳቱን በሽታ የመከላከል አቅም ያዳክማሉ።