ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
በእንግሊዝ የሶስት ዓመት ጨቅላ ላይ አሲድ የደፉ ሶስት ግለሰቦች ታሰሩ
የሶስት ዓመት ጨቅላ ላይ አሲድ በመድፋት አሰቃቂ ጉዳት አድርሰዋል የተባሉ ሶስት ግለሰቦችን የእንግሊዝ ፖሊሶች በቁጥጥር ስር አውለዋል።
የማዕከላዊ እንግሊዝ ዎርሲስተር ግዛት ፖሊሶች እንደተናገሩት ሶስቱ ተጠርጣሪዎች ሆነ ብለው ጨቅላውን አጥቅተዋል።
ጥቃቱ የተፈጸመው ቅዳሜ እለት ሆም ባርጌንስ በተባለ መገበያያ መደብር አቅራቢያ ነበር።
የጨቅላው ቤተቦች በህጻናት ጋሪ ውስጥ ልጃቸውን አስቀምጠው በነበረበት ወቅት የ 22፣ የ 25 እና የ 26 እድሜ ያላቸው ተጠርጣሪዎች ጨቅላው ላይ አሲድ ደፍተዋል።
ጨቅላው ፊቱና ክንዱ ላይ ጉዳት ደርሶበት ወደ ህክምና መስጫ ተወስዷል። ለጊዜው ወደቤቱ ቢመለስም የአሲድ ጥቃቱ ለዘለቄታው የሚያስከትልበት ጉዳት አልታወቀም።
ተጠርጣሪዎቹ አሰቃቂ አካላዊ ጉዳት ለማድረስ በመመሳጠር በሚል ክስ ለንደን ውስጥ ታስረዋል።
ሶስቱ ግለሰቦች ጨቅላው ላይ አሲድ የደፉበት ምክንያት እስከአሁን አልታወቀም።
ቶኒ ጋርነር የተባሉ መርማሪ እንዳሉት የጥቃቱ ዜና ከተሰማበት ቅጽበት አንስቶ የአካባቢው ማህበረሰብ መረጃ በማቀበል ተጠርጣሪዎቹ እንዲያዙ ተባብሯል።
በርካቶች ኢሰብአዊውን ጥቃት እየኮነኑ ይገኛሉ።
"ጨቅላ ላይ እንዲህ ያለ ጥቃት መፈጸም ያስጸይፋል። ጥቃቱ መላው አለምን የሚያስደነግጥም ነው" ሲሉ መርማሪውን ሀዘኔታቸውን ገልጸዋል።