የኦባማ ሠዓሊ የፕሬዚዳንት ሳህለወርቅን ጨምሮ የሌሎች የአፍሪካ መሪዎችን ሥዕሎች ለዕይታ አቀረበ

የፎቶው ባለመብት, Tanguy Beurdeley
የአሜሪካን የቀድሞ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ምስል (ፖርትሬት)ን በመሳል ዝናን ያተረፈው ኬሂንዴ ዋይሊ የኢትዮጵያን ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴን ጨምሮ ሌሎች የአፍሪካ መሪዎችን የሚያሳዩ የጥበብ ሥራዎቹን በፈረንሳይ ለዕይታ አቀረበ።
ኬሂንዴ በባራክ ኦባማ ሥራው የአሜሪካን መሪ ፕሬዚዳንታዊ ምስል (ፖርትሬት) በመሳል የመጀመሪያው አፍሪካዊ አሜሪካዊ በመሆንም ታሪክ ሰርቷል።
በአሁኑ ወቅት 11 የአፍሪካ መሪዎችን የሚያሳዩ የሥዕል ሥራዎቹን ለዕይታ አቅርቧል።
ከኢትዮጵያዋ ፕሬዚዳንት በተጨማሪ የጋናው ፕሬዚዳንት ናና አኩፎ አዶ፣ የናይጀሪያው የቀድሞ ፕሬዚዳንት ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ በመሪዎቹ ምስሎች (ፖርትሬት) ሥዕሎች ከተካተቱበት ይገኙበታል።
‘ኤ ሜዝ ኦፍ ፓወር’ የሚል ርዕስ የተሰጠው የሥዕል አውደ ርዕዩም በፈረንሳይዋ መዲና ፓሪስ በሚገኘው ‘ሙዜ ዱ ኬ ብራንሊ- ጃክ ዢራክ’ ሙዚየም ለዕይታ ቀርቧል።

የፎቶው ባለመብት, Tanguy Beurdeley
አውደ ርዕዩም እስከ መጪው የአውሮፓውያኑ ዓመት ጥር 2024 ድረስ ክፍት ሆኖ ይቆያል ተብሏል።
ኬሂንዴ የመሪዎቹን ምስሎች (ፖርትሬት) ሥዕሎችን ለመሳል 10 ዓመታትን እንደፈጀበት ስለ ጥበብ ሥራዎቹ በተዘጋጀ ዘጋቢ ፊልምም ላይ ተናግሯል።
ከአውሮፓውያኑ 2012 ጀምሮ በተለያዩ የአፍሪካ አገራት በመዘዋወር ከተለያዩ መሪዎች ጋር ተገናኝቷል።
እንዲሁም ከ17ኛው እስከ 19ኛው ክፍለ ዘመን ስለነበሩ የነገስታት፣ የመኳንንት እና ወታደራዊ ሥዕሎችን አጥንቷል እንዲሁም ውይይት አድርጓል።
በተለያዩ የአፍሪካ አገራት ያደረጋቸው ውይይቶች እና ጥናቶች ላይ መሰረት በማድረግም ነው የመሪዎቹን ምስል (ፓርትሬት) የሳለው። እነዚህ ሥዕሎች በዘመኑ የአፍሪካ መሪ መሆን ምን ማለት እንደሆነም ያሳያሉ።
“ሥዕሎቼ የመሪነትን ሥፍራን ነው የሚያሳዩት። ተመልካቾች የዕይታ አድማሳቸውን አስፍተው በአፍሪካ ውስጥ ያለውን ጥበብ፣ አፍሪካን ማዕከል በማድረግም ሥልጣንን እንዲመለከቱ የቀረበ ግብዣ ነው” ብሏል።

የፎቶው ባለመብት, Tanguy Beurdeley












