በሶማሊያ ኤልኒኖ ባስከተለው ጎርፍ ሳቢያ አንድ ሚሊዮን ነዋሪዎች ተፈናቀሉ

በሶማሊያ ኤልኒኖ በተሰኘው ከባድ የአየር ክስተት ምክንያት ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሰዎች ቤት ንብረታቸውን ጥለው ለመፈናቀል መገደዳቸውን የሀገሪቱ ባለስልጣናት ተናግረዋል።

ከሁለት አስርት አመታት በላይ ከሚሆን ጊዜ በኋላ የጣለው ከባድ ዝናብ በአፍሪካ ቀንድ ከፍተኛ ውድመት፣ መፈናቀል እና ሞትን አስከትሏል።

ሶማሊያ በዚህ ክስተት እየተፈተነች ባለችብት ወቅት በዱባይ የዓለም መሪዎች በአየር ንብርት ለውጥ ላይ ለመምከር ተሰባስበዋል።

ለረዥም ጊዜ ከቆየ ድርቅ እየተላቀቀ የነበረው አካባቢው ወቅቱን ባልጠበቀ ከባድ ዝናብ ምክንያት በደቡባዊ ኢትዮጵያ፣ ሶማሊያና ኬኒያ ቢያንስ 270 ሰዎች ስለመሞታቸው ተዘግቧል

በሶማሊያ ብቻ በደራሽ ጎርፍ ከ100 በላይ ሰዎች ሞተዋል።

ሁሉም ከተሞች ሊባል በሚችል ደረጃ በውሃ የተጥለቀለቁ ሲሆን ከፍተኛ ቁጥር ያለው ህዘብ ቤቱን ጥሎ መጠለያ ፍለጋ እንዲወጣ አድርጓል።

በዚህም ሳቢያ ሀገሪቱ እጅግ ፈታኝ በሆነ ሁኔታ ውስጥ ትገኛለች ሲሉ ፕሬዝደንት ሀሰን ሼክ ሞሀመድ ተናግረዋል።

በተመሳሳይ ኢትዮጵያና ኬንያም ከፍተኛ መጠን ያለው ጎርፍን እያስተናገዱ ነው። ከባድ ዝናብ እስከ ቀጣዩ ወር መጨረሻ እንደሚቀጥል በመተንበዩ ይህ ክስተት እንደሚቀጥል ይጠበቃል።

ይህ ከባድ የአየር ሁኔታ በቀጠናው የምግብ ዋስትና ቀውስ እንዲፈጠር ሰበብ ሊሆን እንደሚችል የዓለም ምግብ ፕሮግራም አሳስቧል።

በተጨማሪም የኮሌራ ወረርሽኝ እንዳይፈጠርም ስጋት ፈጥሯል።

የዓለም መሪዎች በሚሰባሰቡበት የዱባዩ የኮፕ28 ጉባዔ ላይ ይመክራሉ። በዚህ ወቅት እንደ በአፍሪካ ቀንድ ያሉ ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ ያላቸው አስተዋጽኦ አነስተኛ ሆኖ ሳለ የከፋ ጉዳት እያስተናገደ ነው ሲሉ ተሟጋቾች እና የሰብዓዊ እርዳታ ድርጅቶች ጥሪ እያቀረቡ ነው።