ከስልጣን የተወገዱት ፕሬዝዳንት ባዙም ለማምለጥ ሙከራ ማድረጋቸውን የኒጀር ጁንታ አስታወቀ

በኒጀር የተመሠረተው ወታደራዊ መንግሥት ከስልጣን በኃይል የተወገዱት ፕሬዝዳንት ሞሐመድ ባዙም ከእስር ለማምለጥ ያደረጉትን ሙከራ ማክሸፉን አስታወቀ።

የቀድሞው ፕሬዝዳንት ከቤተሰቦቻቸው፣ ከምግብ አብሳዮቻቸው እና ከጠባቂዎቻቸው ጋር በለሊት ለማምለጥ ሞክረዋል ሲል የጦሩ ቃል አቀባይ ተናግረዋል።

በሄሊኮፕተሮች ከአገር ለመውጣት ተይዞ የነበረው ዕቅድ መክሸፉን አስታውቋል።

ሐምሌ መጨረሻ ላይ በራሳቸው የጥበቃ አባላት መፈንቅለ መንግሥት የተፈጸመባቸው ባዙም በቁም እስር ላይ ይገኛሉ።

ኒጀር ሳህል ተብሎ የሚጠራው የአፍሪካ ቀጠና ቁልፍ አካል ናት። ከአትላንቲክ ውቅያኖስ እስከ ቀይ ባህር ድረስ ያላውን የሚሸፍነው ይህ አካባቢ የጂሃዲስቶች ጥቃት እና ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥታት ተደጋግሞበታል።

በቀድሞ ፕሬዝዳንት ለማምለጥ የተደረገው ሙከራ ሐሙስ ለሊት 9 ሰዓት አካባቢ መሆኑን የጦሩ ቃል አቀባይ አማዱ አብድራማኔ ለመንግሥታዊው ቴሌቪዥን ተናግረዋል።

"ከስልጣን የተወገዱት ፕሬዝደንት ሞሐመድ ባዙም እና ቤተሰባቸው፣ ሁለቱ ምግብ አብሳዮቻቸው እና ሁለት የጥበቃ አባላቶቻቸው ከታሰሩበት ቦታ ለማምለጥ ሞክረዋል" ብለዋል።

ለማምለጥ ተደረገው ሙከራ ከመክሸፉም በላይ "ዋና ተዋናዮቹ እና ተባባሪዎቻቸው" በቁጥጥር ስር መዋላቸውን አክለዋል።

በዕቅድ መሠረት ባዙም ከዋና ከተማዋ ኒያሜ ወጣ ብሎ ወደሚገኝ መደበቂያ ቦታ ለመሄድ አስበው እንደነበር አብድራማኔ ተናግረዋል።

በመቀጠልም “የውጭ ኃይሎች ንብረት በሆኑ” ሄሊኮፕተሮች ወደ ናይጄሪያ ለመብረር አቅደውም ነበር በማለት የባዙምን ድርጊት “ኃላፊነት የጎደለው ” ሲሉ አውግዘዋል።

የቀድሞው ፕሬዝደንት እና ባልደረቦቻቸው አሁን የት እንደታሰሩ ግልጽ አይደለም። በጉዳዩ ዙሪያም ምርመራ ተጀመሯል።

ባለፈው ሐምሌ የኒጀር ጦር በዲሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጡትን ፕሬዝደንት በመፈንቅለ መንግሥት ከስልጣን አስወገዷል።

በጎረቤት አገራት ቡርኪና ፋሶ እና ማሊ ተመሳሳይ ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥቶች ተካሂደዋል። በአካባቢው የእስላማዊ ታጣቂዎች እና በቫግነር በኩል ደግሞ የሩሲያ ተጽዕኖ እየጨመረ ይገኛል።

ባዙም በይፋ ስልጣናቸውን ለመልቀቅ ፈቃደኛ አልሆኑም።

በቁም እስር ላይ ቢሆኑም በዋሽንግተን ፖስት ላይ ባሳተሙት ጽሁፍ መታገታቸውን እና መፈንቅለ መንግሥቱ "በአገራችን፣ በቀጠናችን እና በመላው ዓለም ላይ አስከፊ መዘዝ ያስከትላል" ሲሉ ገልጸዋል።

ባዙም ከስልጣን ከተወገዱ በኋላ አሜሪካው ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን “በፍጥነት እንዲፈቱ” እና “ኒጀርን በጠንካራ ሥራ ያሳካችው ዲሞክራሲ እንዲጠብቅ” ጥሪ አቅርበዋል።

የምዕራብ አፍሪካ ሃገራት ቡድን የሆነው ኢኮዋስ የመፈንቅለ መንግስቱ መሪዎች ስልጣን እንዲለቁ የሰጠው ቀነ ገደብም አብቅቷል።

ኢኮዋስ ያቀደው ወታደራዊ ጣልቃገብነት ካለመሳካቱም በላይ፤ ጁንታው ፕሬዚዳንቱን እንዲፈታ የቀረቡለትን ጥያቄዎች ችላ ማለቱን ቀጥሏል።

የባዙም ፓርቲ እና የቤተሰብ አባላት ምንም አይነት የውሃ፣ የመብራት እና ትኩስ ምግብ አንዳላገኙ ተናግረዋል።