የአእላፋት ዝማሬ: በገና ዋዜማ በመስቀል አደባባይ የተካሄደው ሥነ ሥርዓት በምሥል

የፎቶው ባለመብት, aelafat zemarie
በየዓመቱ ለገና በዓል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ሥር የኢትዮጵያዊው ጀንደረባ ትውልድ ማኅበር የሚያዘጋጀው የአእላፋት ዝማሬ ሥነ ሥርዓት ታኅሳስ 28/2018 ዓ.ም. ለሦስተኛ ጊዜ ተካሂዷል።
ይህ በመስቀል አደባባይ የተካሄደው መንፈሳዊ ዝግጅት የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባን ጨምሮ የበርካቶችን አድናቆት አግኝቷል።
በዝግጅቱ ላይ የተዋጣላቸው ድንቅ መንፈሳዊ ዝማሬዎች እና ማራኪ ትዕይንቶች ቀርበውበታል።

የፎቶው ባለመብት, aelafat zemarie
በገና በዓል ዋዜማ ለሦስት ዓመታት ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን የእምነቱ ተከታዮችን በማሳተፍ የሚካሄደው ይህ መንፈሳዊ የአደባባይ ዝግጅት በዚህ ዓመት ከቀደሙት በተለየ በአዲስ አበባ ከተማ መስቀል አደባባይ በደማቅ ሥነ ሥርዓት ተካሂዷል።
ባለፉት ሁለት ዓመታት በቦሌ መድኃኒዓለም ቤተክርስቲያን የተካሄደ ሲሆን፣ አሁን በከተማዋ ትልቁ በሆነው መስቀል አደባባይ በነጫጭ አልበሳት የተዋቡ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነት ተከታዮች የኢየሱስ ክርስቶስን ልደት ዋዜማ በተለየ ሥነ ሥርዓት አክብረውታል።

የፎቶው ባለመብት, aelafat zemarie
ይህ ዝግጅት ለመጀመሪያ ጊዜ በብሔራዊ ቴሌቪዥን እና በሌሎችም የቴሌቪዥን ጣቢያዎች እንዲሁም በበርካታ የማኅበራዊ ሚዲያ መድረኮች ላይ በቀጥታ ሲተላለፍ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሕዝብ ተመልክቶታል።
ዓመታዊው የአእላፋት ዝማሬ የኢየሱስ ክርስቶስን ልደት ለማክበር እጅግ በጣም ብዙ ምዕመናን የሚታደሙበት እና መነሻውም "ኢየሱስ በተወለደበት ጊዜ መላዕክት እና እረኞች ያሰሙትን ዝማሬ መሠረት በማድረግ" ታዳሚው ከመመልከት ባሻገር በጸሎት እና በዝማሬው ተሳታፊ እንዲሆን የሚያደርግ መሆኑን አዘጋጆቹ ገልጸዋል።

የፎቶው ባለመብት, aelafat zemarie
በገና በዓል ዋዜማ በሚካሄደው የአእላፋት ዝማሬ ላይ የሚሳተፉ ታዳሚዎች የሚያጠኗቸው የቤተ ክርሥቲያኗን ሥርዓት እና ደንብ የተከተሉ ዝማሬዎች ቀደም ብሎ በተለያዩ የበይነ መረብ መድረኮች ላይ ስለሚቀመጡ በቀላሉ እንዲያገኙት ይደረጋል።
የኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ትውልድ ማኅበር እንደሚለው ማክሰኞ ታኅሣሥ 28/2018 ዓ.ም. በተካሄደው የአእላፋት ዝማሬ ሥነ ሥርዓት ላይ ከ200 ሺህ በላይ ሰዎች በመስቀል አደባባይ ታዳሚ ሆነው ነበር።

የፎቶው ባለመብት, aelafat zemarie
በአገሪቱ ከሚገኙ ዋና ዋና የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ቀዳሚ ሽፋን ያገኘው ይህ የአእላፋት ዝማሬ ዝግጅትን የሚያሳዩ ድንቅ ቪዲዮዎች እና ምሥሎች በሁሉም የማኅበራዊ ሚዲያ መድኮች ላይ በስፋት እየተጋሩ ይገኛሉ።
በተለያዩ አካባቢዎች ሆነው ዝግጅቱን የተመለከቱ በርካታ ሰዎች ሥነ ሥርዓቱ የፈጠረባቸውን ስሜት እና አድናቆት ሲገልጹ ነበር።

የፎቶው ባለመብት, aelafat zemarie
የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ "የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓልን በማስመልከት በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የተካሄደው "የአእላፋት ዝማሬ" ድንቅ ነው" በማለት ከተማዋንም እንዳደመቃት ምስክርነት ሰጥተዋል።

የፎቶው ባለመብት, aelafat zemarie
በትልቁ የአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ የተሰናደው ሥነ ሥርዓት በአግባቡ የታሰበበት እና የተዘጋጀ በሥርዓት የተመራ መሆኑ ብዙዎችን አስደንቋል።

የፎቶው ባለመብት, aelafat zemarie
በቪዲዮዎች እና በፎቶግራፎች ላይ እንደታየው የመድረኩ ዝግጅት የታዳሚው ቦታ አያያዝ የሥነ ሥርዓቱ ቅደም ተከተል ማራኪ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት አድርጎት የበርካቶችን ቀልብ ስቧል።
*ሁሉም ፎቶዎች የአእላፋት ዝማሬ አዘጋጅ ከሆነው የኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ትውልድ ማኅበር በተገኘ ፈቃድ የቀረቡ ናቸው።















