በቃፍታ ሸራሮ ፓርክ ኤፍኤምዲ የተባለ በሽታ የዱር እንስሳትን እየገደለ ነው

በቃፍታ ሸራሮ ፓርክ ኤፍኤምዲ (ፉት ኤንድ ማውዝ) የሚል መጠሪያ ያለው በሽታ የዱር እንስሳትን በተለይ ደግሞ አጋዘን እየገደለ እንደሆነ ታውቋል።

በበሽታው ምን ያህል ቁጥር ያላቸው አጋዘኖች እንደሞቱ ለማወቅ ባይቻልም በአካባቢው የሚገኘው የቢቢሲ ዘጋቢ እንዳረጋገጠው በርካቶች ሞተዋል፤ በርከት ያሉትም ታመዋል።

የፓርኩ ባለሞያ ሃፍቶም ሐጎስ ለቢቢሲ እንደገለፁት በሽታው የዱር እንስሳትን እንዲሁም ቤት እንስሳትን ያጠቃል።

በቀላሉም የሚተላለፍ ሲሆን እስካሁን ባለው የዱር እንስሳት ብቻ እንደተጠቁ ባለሞያው ተናግረዋል።

በበሽታው የተጠቃ እንስሳ ጆሮውና መቀመጫው ላይ የመቁሰል ምልክት ይታይበታል ተብሏል።

በምዕራብ ትግራይ የሚገኘው ቃፍታ ሸራሮ ፓርክ ከ200 ሺሕ ሄክታር በላይ ስፋት ያለው መሬት የሚሸፍን ሲሆን፤ በርካታ ዓይነት የዱር እንስሳትና ዕፅዋትም ይገኙበታል።

በተለይም ዝሆንና አጋዘን በብዛት የሚኖሩበት ነው።

ከሰሞኑ በአካባቢው የእሳት ቃጠሎ ተንስቶ ከ1500 በላይ ሄክታር መሬት ላይ ውድመት አስከትሏል።

ባለፈው ሰኞ አመሻሽ ላይ በፓርኩ የተነሳው የእሳት ቃጠሎ ከትናንት ወድያ ጥቅምት 26፣2012 ዓ.ም በቁጥጥር ማዋል ቢቻልም፤ በተመሳሳይ ቀን ዓዲ ጎሹ በተባለ ሌላ ኣቅጣጫ እንደ አዲስ የተነሳው ቃጠሎ ጉዳት እንዳደረሰ በአከባቢው የሚገኘው ሪፖርተራችን ታዝቧል።

ፓርኩ በፌደራል መንግሥት ስር የሚተዳደር ቢሆንም አጥር እንደሌለውና በበጎ ፈቃደኝነት ተሰማርተው የሚሰሩ ሰዎች ቁጥርም በቂ እንዳልሆነም ተገልጿል።

በተለያዩ ጊዜያቶች በተደጋጋሚ የእሳት ቃጠሎ እንደሚነሳና የአካባቢው ታጣቂዎች (ሚሊሻ) ገብተው እርዳታ እንደሚያደርጉ ለማወቅ ተችሏል።

በአካባቢው የሚነሳው ቃጠሎ በአብዛኛው በፓርኩ ውስጥ ወርቅን በማውጣትና ማርን በመቁረጥ የተሰማሩ እረኞች የሚያስነሱት እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል።