በትግራይ የተመጣጠነ ምግብ እጥረት "በከፍተኛ ሁኔታ" እየጨመረ ነው ተባለ

የፎቶው ባለመብት, AFP
በትግራይ የተመጣጠነ ምግብ እጥረት "በከፍተኛ ሁኔታ" እየጨመረ መሆኑን ድንበር የለሹ የሐኪሞች ቡድን ገለጸ።
የዓለም አቀፉ ድንበር የለሽ ሐኪሞች ቡድን ሪፖርት በትግራይ ክልል በከፍተኛ ሁኔታ በምግብ እጥረት የተጎዱ ታዳጊዎችን ማግኘቱን ይፋ አድርጓል።
የዓለም ምግብ ድርጅት በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ በትግራይ 91 በመቶ የሚሆነው ሕዝብ የአስቸኳይ የምግብ እርዳታ ፈላጊ ነው ሲል አስታውቋል።
የተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክር ቤት በኢትዮጵያ የትግራይ ክልል በቂ የሰብዓዊ እርዳታ ባይቀርብም የኢትዮጵያ መንግሥት ጥረት ግን የሚበረታታ ማለቱ ይታወሳል።
የተባበሩት መንግስታት የሰብዓዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ቢሮ (ኦቻ/OCHA) ሚያዝያ 4 ቀን 2013 ዓ.ም ትግራይን በተመለከተ ባወጣው ሪፖርት በክልሉ የተፈጠረውን ሁኔታ ተከትሎ ከፍተኛ የሰብዓዊ ቀውስ መከሰቱን አስታውሷል።
ኤም ኤስ ኤፍ እንዳለው ከሆነ በትግራይ ገጠራማ አካባቢ በሚገኙ ክልኒኮች ክትትል ከተደረገላቸው ሕጻናት መካከል ሶስት እጅ የሚሆኑት በምግብ እጥረት ተጎድተዋል።
ድርጅቱ አክሎም የእለት እርዳታ ከዋና ከተማዎች በዘለለ ወደ ገጠሪቱ የትግራይ ክፍል የሚደርሰው በአነስተኛ መጠን መሆኑን ገልጿል።
አንዳንድ ቤተሰቦች በቀን አንዴ ይመገባሉ ያለው ሪፖርቱ በብዛት ዳቦ ብቻ እንደሚበሉም አክሏል።
ድንበር የለሽ የሃኪሞች ቡድን እንደገለፀው የዝናቡ ወቅት እየደረሰ ሲመጣ የሚካሄደው ጦርነት ገበሬዎችን ወደ ማሳቸው ከመሄድ በመከልከል ሁኔታው እየከፋ ሊመጣ እንደሚችል ተንብይዋል።
በትግራይ እስካሁን ድረስ ከፍተኛውን የሰብዓዊ እርዳታ የሚያቀርበው መንግሥት መሆኑን ከዚህ ቀደም መግለፁ ይታወሳል።
የሕፃናት የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ከቦታ ቦታ ቢለያይም ባለፉት ወራቶች አጣዳፊ የተመጣጠነ ምግብ እጥረት በትግራይ እየጨመረ መምጣቱን የድንበር የለሹ ሐኪሞች ድንገተኛ ቡድን አስተባባሪ ቶማሶ ሳንቶይናገራሉ።
ብዙ ቤተሰቦች የሚገኙበት የምግብ ጥራት እና ብዛት መቀነሱ ብዙዎች በቀን አንድ ጊዜ ብቻ መመገባቸውን በምክንያትነት አቅርበዋል፡፡
"በክልሉ የሰብአዊ ዕርዳታን ለማሳደግ እና ተደራሽነቱን ለማስፋፋት የሚጠይቅ አስቸኳይ ፍላጎት አለ" ብለዋል ሳንቶ።
ድንበር የለሹ የሐኪሞች ቡድን በአሁኑ ወቅት በአዲግራት፣ አክሱም፣ አድዋ፣ አቢ አዲ፣ ሽሬ፣ ሸራሮ፣ ሁመራ እና ዳንሻ ከተሞች የህክምና አገልግሎት እየሰጠ ነው። ከ 2021 መጀመሪያ ጀምሮ የተንቀሳቃሽ ቡድኖቹን እንቅስቃሴ ወደ ገጠር ከተሞች እና ተራራማ አካባቢዎች እያስፋፋሁ ነው ብሏል።
ከዚህ ቀደም የኢትዮጵያ መንግሥት ለትግራይ ክልል ከውጭ የሰብዓዊ እርዳታ ድርጅቶችና ሀገራት በኩል የሚጠበቀው እርዳታ በጊዜ ባለመድረሱ 40 ቢሊዮን ብር ወጪ ማድረጉን አስታወቆ ነበር።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ የሰብዓዊ ዕርዳታ ሰጪ ድርጅቶች ከዚህ ቀደም ያጋጥማቸው የነበረውን ረዥም የፈቃድ አሰጣጥ ሂደት በማቃለል አሁን በትግራይ ክልል ለመንቀሳቀስ ለሚመለከተው አካል በማሳወቅ ብቻ ዕርዳታውን ለተጠቃሚዎች ማዳረስ የሚችሉ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
ራቅ ብለው በሚገኙ እና አመቺ ሁኔታ በሌለባቸው የተወሰኑ አከባቢዎችም ጭምር ዕርዳታውን ለማዳረስ በሲቪልና ወታደራዊ በቅንጅት የሚሰራበት ሁኔታ እንደተመቻቸ አሳውቀዋል፡፡
ሚኒስትሩ በገለጻቸው ለ3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዜጎች ዕርዳታውን ማድረስ መቻሉ፤ ከተሰራጨው ዕርዳታ ውስጥ 70በመቶ በመንግሰት መሸፈኑን ጨምረው አስረድተው ነበር።












