ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ፀሐይን ተጠግታ የምታልፈው መሣሪያ በሳይንቲስቶች ዘንድ ጉጉትን ፈጥራለች
የአውሮፓ ሥርዓተ ፀሐይ ጥናት ማዕከል (ሶሎ) ወደ ህዋ የላካት አነስተኛ የምርምር መሣሪያ ዛሬ ሰኞ ፀሐይን በቅርብ ርቀት ተጠግታ ታልፋለች ተብሎ እየተጠበቀ ነው፡፡
ይቺ የምርመራ አንቴና ፀሐይን በቅርብ ርቀት ተጠግታ አለፈች የሚባለው 77 ሚሊዮን ኪሎ ሜትር ከፀሐይ ርቃ መሾር ስትችል ነው። መድር በምህዋሯ ላይ ፀሐይን እየዞረች ያለችው በአማካይ 149 ሚሊዮን ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ሆና ነው፡፡
የዚህች አንቴና መሰል መሣሪያ ዓላማ የከዋክብትን ባህሪ ማጥናት ሲሆን፤ በተለይ ከዋክብት ከፀሐይ ጋር ያላቸውን መተስተጋብር ለመተንተን የሚያስችል መረጃ በመቃረም ወደ ምድር ታቀብላለች ተብሏል፡፡
በቬኑስና ሜርኩሪ መካከል ባለ ምህዋር ትሾራለች የተባለችው ይቺ መሣሪያ ወደ ህዋ የመጠቀችው ባለፈው ጥቅምት ወር ላይ ነበር፡፡
ሶሎ የሚል ስም ያላት ይቺ መሣሪያ በጊዜ ሂደት ወደ ፀሐይ እየተጠጋች በመሄድ ከፀሐይ ጋር የሚኖራት ርቀት 43 ሚሊዮን ኪሎ ሜትር ብቻ የሚሆንበት አጋጣሚ ይኖራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
በሥርዓተ ፀሐይ ውስጥ በዚህን ያህል ወደ ሥርዓተ ፀሐይ ጠልቆ ለመግባት ሶሎ አምስተኛዋ ናት፡፡ ከዚህ ቀደም ማሪነር 10፣ ሄሊዮስ 1 እና 2፣ ሜሴንጀር እና የሜሪካኑ ፓርከር ሶላር ፕሮብ ፀሐይን በመጠጋት ባህሪዋን ለማጥናት ሞክረዋል፡፡
ሶሎ የአውሮፓ የሥርዓተ ፀሐይ ኤጀንሲ ንብረት ስትሆን የተገጣጠመችውም በዩናይትድ ኪንግደም የኤሮስፔስ ኩባንያ በሆነው ኤርበስ ነው፡፡
ሶሎ ከመጠቀችበት ጊዜ ጀምሮ ባለፉት አራት ወራት ጠቅላላ አሰሳና ራሷንና የተገጠሙላት መሣሪያዎች ምን ያህል ጤናማ እንደሆኑ በመፈተሸ ላይ ቆይታለች፡፡
እንደዚህ ዓይነት ወደ ህዋ የሚመጥቁ መሣሪያዎች ወደፊት መሬታችን ምን ዓይነት የአየር ንብረት ይኖራታል፤ የፀሐይና ሌሎች በአካባቢው የሚገኙ ከዋክብት መስተጋብር ምንድነው ለሚለው እጅግ ወሳኝ ጥያቄዎች መረጃን ያቀብላሉ፡፡