በኮሮናቫይረስ፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ቻይና የሚያደርገውን በረራ እንደማያቋርጥ ገለጸ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
በአፍሪካ ትልቁ የሆነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ምንም እንኳን ግፊት ቢደረግበትም ወደቻይና የሚያደርገውን በረራ እንደማያቋርጥ በድጋሚ አሳወቀ።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገብረማሪያም እንደተናገሩት የኮሮናቫይረስ መስፋፋትን ለመቆጣጠር ወደ ቻይና የሚደረጉ በረራዎችን ማቋረጥ መፍትሄ አይሆንም ሲሉ ተናግረዋል።
አክለውም በቫይረሱ ምክንያት ቻይናን ማግለል ፍትሃዊ አይደለም ብለዋል።
"የቀጥታ በረራዎችን ማቋረጥ ቫይረሱን አይገታውም፤ ምክንያቱም ተጓዦች ከቻይና ከሌሎች አገራት በኩል ኢትዮጵያን ጨምሮ ወደሌሎቹ የአፍሪካ አገራት ይገባሉ። በዚህም ነው ዓለም እርስ በርሷ ተሳስራላች የሚባለው" ሲሉ መናገራቸውን የቻይናው ዢንዋ የዜና ወኪል ዘግቧል።
አቶ ተወልደ በተጨማሪም እንደጠቀሱት በኮሮና ቫይረስ ምክንያት እንደሌሎቹ አየር መንገዶች ሁሉ የገቢ መቀነስ አጋጥሞታል። በዚህም የተጓዦች ቁጥር በ20 በመቶ ቀንሷል ብለዋል።
ስለዚሁ ጉዳይ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገብረ ማሪያም ከሳምንታት በፊት በሰጡት ምላሽ "አሁን ጊዜያዊ ችግር ስላጋጠማቸው በረራ ማቋረጥ በሞራልም በሥነ ምግባርም ተቀባይነት የለውም" በማለት የተከሰተውን ችግር ለመከላከልም "ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ እንጂ፤ በረራዎችን ማቋረጥ ግን ካሉ አማራጮች ውስጥ አይደለም" ሲሉም ተናግረዋል።
ባለፈው ሳምንት በተጠናቀቀው የፈረንጆቹ የካቲት ወር ላይ ብቻ በኮሮናቫይረስ ምክንያት የአፍሪካ አየር መንገዶች 400 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማጣታቸውን ዓለም አቀፉ የአየር ትራንስፖርት የበላይ ተቆጣጣሪ አስታወቀ።
ምንም እንኳን የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ እንደሌሎቹ አህጉራት አፍሪካን ክፉኛ ባያጠቃም ያስከተለው ተጽእኖ ግን ቀላል የሚባል እንዳልሆነ እየተነገረ ነው።
የወረርሽኙን መከሰት ተከትሎ የታንዛኒያ፣ የሞሪሺየስ፣ የማዳጋስካር፣ የሩዋንዳ፣ የሞሮኮ፣ የግብጽና የኬንያ አየር መንገዶች ወደ ቻይናና ከቻይና ወደ የአገራቸው የሚደረጉ ሁሉንም በረራዎች እንዲቋረጡ አድርገዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ቻይና የሚያደርገውን በረራ እንደማያቋርጥ ገለጸ

ዓለም አቀፉ የአየር ትራንስፖርት ማኅበር እንደሚለውም ከኮሮናቫይረስ መስፋፋት ጋር በተያያዘ አየር መንገዶቹ 400 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ ኪሳራ እንዳጋጠማቸው አመልክቷል።
ለዚህም እንደ ምክንያት የተጠቀሰው አየር መንገዶቹ ወደ ቻይና የነበሯቸውን የበረራ መስመሮች በማቋረጣቸውና በረራዎችን በመሰረዛቸው እንደሆነ ተገልጿል።
የዓለም አቀፉ የአየር ትራንስፖርት ማኅበር ምክትል ፕሬዝዳንት ለቢቢሲ እንደተናገሩት በተለይ ባለፈው የፈረንጆች ዓመት 100 ሚሊዮን ዶላር ኪሳራ ላጋጠማቸው የአፍሪካ አየር መንገዶች የኮሮናቫይረስ ክስተት የገጠማቸውን ችግር የበለጠ የከፋ ያደርግባቸዋል።
እስካሁን ድረስ በግብጽ፣ በቱኒዚያ፣ በሞሮኮ፣ በአልጄሪያ፣ በናይጄሪያና በሴኔጋል በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች መገኘታቸው የተዘገበ ቢሆንም በየትኛውም የአፍሪላ አገር ውስጥ በሽታው በወረርሽኝ ደረጃ አልተከሰተም ተብሏል።
የዓለም የጤና ድርጅት እንዳስጠነቀቀው ደካማ የጤና አገልግሎት ሥርዓት ያላቸው ድሃ አገራት ወረርሽኙን ለመቋቋም አቅም የላቸውም፤ ከእነዚህ ውስጥም አብዛኞቹ የሚገኙት በአፍሪካ ውስጥ መሆኑ አሳሳቢ ነው ብሏል።
በተያያዘ ዜና የኬንያ መንግሥት ከኮሮናቫይረስ የመስፋፋት ስጋት ጋር በተያያዘ ከሰሜናዊ የጣሊያን ሁለት ከተሞች የሚመጡ በረራዎች እንዲቋረጡ አዟል።
ኬንያ ይህንን እርምጃ የወሰደችው በአውሮፓ ውስጥ በርካታ ቫይረሱ የተገኘባቸው ታማሚዎች ካሉባት አገራት አንዷ ከሆነችው ጣሊያን የመጡ መንገደኞች አፍሪካ ውስጥ በበሽታው ተይዘው በመገኘታቸው ነው።
በቱኒዚያ፣ በሞሮኮና ናይጄሪያ ውስጥ በቫይረሱ ተይዘው የተገኙት ሰዎች ከጣሊያን የመጡ መሆናቸው ስጋት መፍጠሩን ተከትሎ ነው የኬንያ መንግሥት ናይሮቢ ከሚገኘው የጣሊያን ኤምባሲ ጋር በመመካከር ነው የተወሰኑ በረራዎችን ከማቋረጡ ውሳኔ ላይ የደረሰው።
የኬንያ የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ሙታሂ ካግዌ እንደተናገሩት ጣሊያን ውስጥ በበሽታው መያዛቸው የተረጋገጡ ሰዎች ቁጥር ከፍ ማለቱ እዚህ ውሳኔ ላይ እንዲደርሱ አድርጓቸዋል።
ጣሊያን ውስጥ ቢያንስ 1800 ሰዎች በኮሮናቫይረስ መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን 52 ሰዎች ደግሞ በበሽታው ህይወታቸው አልፏል።












