ፆታዋ ያከራከረው ደቡብ አፍሪካዊት ሯጭ በፍርድ ቤት ተረታች

የ800 ሜትር ኦሎምፒክ ሻሚፒዮን የሆነችው የ28 ዓመቷ ደቡብ አፍሪካዊት ሯጭ ካስተር ሰሜንያ ዓለም አቀፉን የአትሌቲክስ ፌደሬሽን የከሰሰችው 'ቴስቶስትሮን' የተሰኘው የወንድ ሆርሞን ከፍ ባለ መጠን ያላቸው ሴት ሯጮችን በተመለከተ ባወጣው ህግ ምክንያት ነበር።

ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፌደሬሽን 'ቴስቶስትሮን' ለሴት ሯጮች ከፍተኛ ጉልበት ስለሚሆን እንደ ሰሜንያ ያሉ ይህ ሆርሞን በከፍተኛ መጠን ያላቸው ሴት ሯጮች በውድድር ፍትሃዊ ያልሆነ ብልጫ ያሳያሉ በሚል ነው በሴት ሯጮች የቴስቶስትሮን መጠን በመድሃኒት መገደብ አለበት የሚል ህግ ያወጣው።

ሰሜንያም ይህ ህግ እንደ ተፈጥሮዬ እንዳልሆን የሚያደርግ ነው በማለት ነበር ጉዳዩን ወደ ዓለም አቀፉ የስፖርት የግልግል ዳኝነት ተቋም የወሰደችው።

ቀደም ሲልም መሮጥ የምትፈልገው ምንም ምንም ሳይባል ተፈጥሮ እንደሰጣት፤ እንደማንነቷ እንደተፈጥሮዋ እንደሆነ ተናግራ ነበር- ሰሜንያ

አሁን ግን ፍርድ ቤቱ ክሱን ውድቅ ስላደረገው እንደ ሰሜንያ ያሉና ከ400 ሜትር ጀምሮ እስከ ማይል የሚሮጡ ሴቶች በህጉ መሠረት በመድሃኒት የወንድ ሆርሞን ማለትም 'ቴስቶስትሮን' መጠናቸውን ለመቀነስ ወይም የሚሮጡበትን መጠን ለመቀየር ይገደዳሉ።

"ለአስር ዓመታት ያህል ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽን ፍጥነቴን ሊገታ ሞክሯል። ይህ ግን እንዲያውም ጠንካራ አደረገኝ" በማለት የአሁኑ የፍርድ ውሳኔም ወደ ኋላ እንደማይዛት ሰሜንያ ተናግራለች።

ዳግም ከዚህ ፍርድ በላይ ከፍ ብላ የደቡብ አፍሪካን እንዲሁም ለዓለም ወጣት ሴቶችና ሯጮች ምሳሌ እንምትሆንም አስታውቃለች።

የስፖርት ግልግል ዳኝነት ፍርድ ቤቱ የዓለም አቀፉ ሩጫ ፌደሬሽን ውሳኔ አድሏዊነት ያለው ሊባል ቢችልም ውሳኔውን ግን "አስፈላጊ፣ ምክንያታዊና ሚዛናዊ" ብሎታል።

ለሌሎች ሴት ሯጮች ውድድሮች ፍትሃዊ እንዲሆኑ ከማድረግ አንፃርም ውሳኔው አስፈላጊ እንደሆነም አስረግጧል።