አፕል ቲቪ፡ አዲሱ የበይነ መረብ ሥርጭቱን ይፋ አደረገ

አፕል

የፎቶው ባለመብት, Apple

ዝነኛ ሰዎች በተካፈሉበት ካሊፎረኒያ ውስጥ በተደረገ ደማቅ ዝግጅት አፕል 'አፕል ቲቪ' የተሰኘውን አዲስ የቴሌቪዥን ስርጭት መጀመሩን ይፋ አደረገ።

ጄኒፈር አኒስተን፣ ስቲቨን ስፒልበርግና ኦፕራ ዊንፍሪ በአፕል ዋና መሥሪያ ቤት አዲሱን ቴሌቭዥን ለማስመረቅ መድረኩን ካደመቁት ታዋቂ ሰዎች መካከል የተሰወሰኑት ነበሩ።

ቴሌቪዥኑ ነባር የኤችቢኦ እና ሁሉ የቴሌቪዥን ይዘቶችን ይዞ እንደሚመጣም ለሕዝብ አሳውቃዋል።

ከቴሌቪዥኑ በተጨማሪ አፕል የክሬዲት ካርድ፣ የጌም መድረክና የተለያዩ መተግበሪያዎችንም ጭምር ለሕዝብ አገልግሎት ይዘው እንደሚመጡ ተነግሯል።

ዝግጅቱ በካሊፎረኒያ ግዛት የተደረገ ሲሆን የአፕል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ቲም ኩክ ከመጀመሪያው ጀምረው ጥሪው አዲስ ዕቃ ይፋ ለማድረግ ሳይሆን አዲስ አገልግሎት ለሕዝብ ለማሳወቅ እንደሆነ ተናግረዋል።

42 ዓመታትን ላስቆጠረው ድርጅት አዲስ አቅጣጫ መሆኑ አይካድም ተብሏል።

ስቲቭ ካሬል፣ ሪስ ዊተርስፑን እና ጄኒፈር አኒስተን

የፎቶው ባለመብት, Apple

የምስሉ መግለጫ, ስቲቭ ካሬል፣ ሪስ ዊተርስፑን እና ጄኒፈር አኒስተን

አፕል ቲቪ

አፕል ቆይቶም ሆነ ዘግይቶ ኔትፍሊክስ እና አማዞን ወደ ተቆጣጠሩት የበይነ መረብ ስርጭት ይገባል ተብሎ ይጠበቅ ነበረ።

የአፕል ቲቪ መተግበሪያ በቅርቡ ለሕዝብ ይፋ እንደሚደረግ ስቲቨን ስፒልበርግ ቀደም ብሎ ፍንጭ ሰጥቶ ነበር።

ስፒልበርግ እራሱ ለእዲሱ የቴሌቪዥን መድረክ አንዳንድ ፕሮግራሞችን እንደሚሠራም ተናግሯል።

በዝግጅቱ መድረክ ላይ እራሳቸውን ካሳዩት መካከል ሪስ ዊተርስፑን፣ ስቲቭ ካሬል፣ ጄሶን ሞሞዋ፣ አልፍሬ ዉዳርድ እና ኮሜዲያን ኩሜል ናንጂያኒ ደግሞም ከሴሰሚ ስትሪት ቢግ በርድ ነበሩ።

መተግበሪያው እንደ ሳመሰንግ፣ ኤልጂ፣ ቪዚዮ፣ አማዞን፣ ሮኩ እና ሶኒ የተሰኙት የተወዳዳሪ መገልገያዎች ላይ ግልጋሎት እንደሚሰጥ ይፋ ተደርጓል።

ኦፕራ ዊንፍሪ

የፎቶው ባለመብት, Apple

የምስሉ መግለጫ, ኦፕራ ዊንፍሪ በአፕል ቲቪ የመጽሐፍ ቡድኗን የማስተላለፍ አጋጣሚ ሊፈጠር እንደሚችልም ፍንጭ ሰጥታለች

ከመጀመሪያው በአፕል ቲቪ ይዘት ውስጥ እንደማይካተት ያሳወቀው ኔትፍሊክስ ያልተገኘበት ዝግጅት ላይ ወርሃዊው ክፍያ አልተነገረም ነበር።

"የአፕል ፈተና አዲሱን አገልግሎት ከተወዳዳሪ አቅራቢዎች ለየት ባለ እና በአዲስ መልኩ ለተገልጋዮች እንደ የኔትፍሊክስ 'ስትሬንጀር ቲንግስ' ማቅረብ እንደሚችል ነው" በኒው ዮርክ ዩኒቨርሲቲ የፊልም ፕሮዳክሽንና ባለሙያ የሆኑት ዶ/ር ኤድ ብራማን ተናግረዋል።

የአፕል ካርድ (የብድር አገልግሎት)

የአፕል ክሬዲት ካርድ

የፎቶው ባለመብት, Apple

የምስሉ መግለጫ, ካርዱ እራሱ ከቲታንየም የተሠራ ሲሆን ለፊርማ እና ለቁጥር ቦታ አልተተወለትም

በተጨማሪም በዚህ ዓመት የክረምት ወቅት የአፕል ክሬዲት ካርድ በአሜሪካ ለሕዝብ አገልግሎት ይቀርባል።

በአይፎን ስልክ ሊገለገሉበት የሚችሉትና እራሱን የቻለ ክሬዲት ካርድ የሚያዘጋጅ ሲሆን እያንዳንዱ ግዢ ላይ በጥሬ ገንዘብ መልስ መቀበል እንዲችሉ ይደረጋል።

"የክሬዲት ካርዱ ክፍያ በሚደረግበት ጊዜ ቀኑ ቢያልፍ የማርፈድ ቅጣት ክፍያ ወይም ዓመታዊ እና ዓለም አቀፍ ክፍያዎች አይኖሩትምም" ይላሉ የአፕል ቲቪ ምክትል ፕሬዚዳንት ጄኒፈር ቤይሊ።

ጎልድመን ሳክስና እና ማስተር ካርድ በእንድ ላይ በመሆን ካርዱን እንደሠሩትም ታውቋል።

የዜና አገልግሎት

አፕል ኒውስ የሚል ሌላ አገልግሎትም ለሕዝብ እንደሚያቀርቡም ተናግረዋል። አፕል ኒውስ እነ ማሪ ክሌር፣ ቮግ፣ ኒው ዮርከር፣ ኤስክዋየር፣ ናሽናል ጄዮግራፊክና ሮሊንግ ስቶንን የመሳሰሉ ከ300 በላይ መጽሔቶችን እንደሚይዝ ተነግሯል።

ኤል ኤ ታይመስ እና ዎል ስትሪት ጁርናልም እንደሚካተቱ አሳውቀዋል።

አክለውም አንባቢያን የሚያነቡትን እራሱ አፕል እንደማይከታተልና ለማስተዋወቂያ ድርጅቶች አሳልፎ እንደማይሰጥ ይፋ አድርጓል።

አፕል ኒውስ በወር 9.99 ዶላር (በዛሬው ምንዛሬ 285 ብር ገደማ) የሚያወጣ ሲሆን ለአሜሪካና ለካናዳ ተገልጋዮች ከአሁን ሰዓት ጀምሮ ክፍት እንደሆነ አሳውቀዋል። ይህ የፈረንጆቹ ዓመት ሳያልቅ ደግሞ ወደ አውሮፓም እንደሚሸጋገር ተናግረዋል።

ከአፕል ቲቪ ለየት የሚያደርገው ይህ አገልግሎት በአፕል መገልገያ መሣሪያዎች ላይ ብቻ መኖሩ ነው።

የ X ይዘትን ይለፉት
ይዘቱን X ይፈቅዳሉ?

ይህ ጽሑፍ በX. የቀረበ ይዘት ይዟል። ገጹ ቴክኖሎጂዎች ወይም ኩኪዎች ሊኖረው ስለሚችል ገጹ ከመከፈቱ በፊት የእርስዎን ፍቃድ እንጠይቃለን። ፍቃድዎን ከመስጠትዎ በፊት የX ኩኪ ፖሊሲ እና የ ማንበብ ይፈልጉ ይሆናል። ይዘቱን ለማንበብ ‘እቀበላለሁ ቀጥል’ የሚለውን ይምረጡ።

ማሳሰቢያ፡ የሦስተኛ ወገን ይዘቶች ማስታወቂያ ሊኖራቸው ይችላል

የ X ይዘት መጨረሻ

ጨዋታዎች (ጌሚንግ)

አፕል አርኬድ

የፎቶው ባለመብት, Apple

የምስሉ መግለጫ, አፕል አርኬድ ሌላ ቦታ የማይገኙ ከ100 በላይ ጨዋታዎችን (ጌሞችን) ያቀርባል

ከመተግበሪያ ገበያው አፕል አርኬድ ከ100 በላይ ጨዋታዎችን ለሕዝብ ግልጋሎት የሚያቀርቡ ሲሆን እነዚህም ጨዋታዎች ያለ በይነ መረብ መጫወት እንደሚቻልም ተናግረዋል።

አገልግሎቱ ለ150 ሃገራት በቅርብ የሚደርሱ ሲሆን የመመዝገቢያው ዋጋ ግን ይፋ አልተደረገም።

እ.አ.አ. በ2018 አይኤችኤስ ማርኬት የተሰኘው ድርጅት አይኦኤስ ማለትም የአፕል የአሠራር ሂደት በጨዋታ ገበያ የ33.5 ቢሊየን ዶላር ገበያ መሆኑን ተናግሯል።

እንደ አፕል አርኬድ ያሉ የጨዋታ መድረኮች በውስጣዊ መተግበሪያ የሚገዙ ወይም ማስተዋወቂያ እንዲይዙ ባለማድረጋቸው ገና ትርፋማ ለመሆን ብዙ ዕድሎችን ሊፈጥር ይችላል በማለት የጨዋታ (ጌም) ተመራማሪና የአይኤችኤስ ዳይሬክተር ፒርስ ሃርዲንፍ ሮልስ ይናገራሉ።

አክሎም "ጨዋታዎቹን ለየት ባለ መልኩ በተጠና ወርሃዊ ክፍያና ለአፕል አርኬድ ብቻ የታሰቡ ጨዋታዎችን ለሕዝብ የማቅረቡ ውሳኔ ለጨዋታው ገበያ ያላቸውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው" በለዋል።

አክለውም "አፕል እንደ ማይክሮሶፍት፣ ፌስቡክ፣ ጉግልና አማዞን ያሉ ድርጅቶች ቀጥተኛ ባልሆነ መልኩ የጨዋታውን ገበያ ሊቀላቀል ነው" ይላሉ።