አዲስ አበባ፡ የፈጠራ ማዕከል ለመሆን እየጣረች ያለች ከተማ

አዲስ አበባ

የፎቶው ባለመብት, EDUARDO SOTERAS

"ወጣት ነኝ፤ ሕልም አለኝ ኢትዮጵያን በቴክኖሎጂ ለመቀየርም ዝግጁ ነኝ" አዲስ አበባ ላይ ከፍትኛ የሥራ ኃላፊዎችና ፖለቲከኞች ለቴክኖሎጂ ትኩረት እንዲሰጡ ሰላም ወንድም የተናገረችው ነው።

የ29 ዓመቷ ወጣት ከ32ኛው የአፍሪካ ሕብረት ጉባዔ ጎን ለጎን በተካሄደ ውይይት ተሞክሮዋን እንድታቀርብ ተጋበዛ "ለሙከራ የሚሆን ደህንነቱ የተጠበቀ ቦታ ያስፈልገናል፤ ይህንን ሥራ ስንሠራ ሙከራውንና ውጤቱን የምናጤንበት" በማለት ለመሪዎቹ አሳስባለች።

ባለፈው ዓመት ጠቅላይ ሚንስትር አብይ አህመድ ወደ ሥልጣን ሲመጡ አንዱ ትኩረት ያደረጉበት ጉዳይ የቴክኖሎጂውን ዘርፍ ማሳደግ ነው። ይህንን ግንዛቤ በማድረግ ሰላምና ሌሎቹ ጓደኞቿ አዲስ አበባን እንደ ናይሮቢ፣ ሌጎስ እና ኬፕ ታውን የአፍሪካ አንዷ የኢኖቬሽን ማዕከል ለማድረግ ተስፋ ሰንቀዋል።

ግማሽ የሚሆነው የአፍሪካ የቴክኖሎጂ ማዕከል የሚገኘው በኬንያ፣ በናይጄሪያ፣ በደቡብ አፍሪካና በጋና ነው። እነዚህ ሃገራት ለቴክኖሎጂ ግኝት ከሚለቀቀው በጀት ሦሰት አራተኛውን ወይም 75% የሚሆነውን ይወስዳሉ።

"ወጣቱ እርሻና ግብርና የጥንት ሥራ ይመስላቸዋልና የወላጆቻቸውንና የአያቶቻቸውን መሬት እየተው ነው" የምትለው ሰላም ወንድም "በይበልጥ በቴክኖሎጂ እንዲታገዝ ብናደርግ ወጣቱ ወደዚያ ሥራ እንዲሰማራ ማድረግ እንችላለን" ትላለች።

ሰላም ወንድም የእራሷ የቢዝነስ ሥራ ግሮሃይድሮ (ሰብልን ያለ አፈር በማደበሪያ ብቻ የሚያሳድግ) የተባለ ሲሆን፤ ማበረታቻ ለማግኘት የሚያስችላትን ሥራ እየሠራች ነው። ግሮሃይድሮ ከብሉ ሙን ውጭ የሆነ መቀመጫውን አዲሰ አበባ ቦሌ አካባቢ ያደረገ የቴክኖሎጂ ግኝት ማበልፀጊያ ነው።

ብሉ ሙን የተባለው ተቋም ደግሞ በዓለም ላይ ያሉ የቴክኖሎጂ አበልፃጊ ተቋማትን ይመስላል።

ሰላም ወንድም

የፎቶው ባለመብት, Thomas Lewton

የምስሉ መግለጫ, ሰላም ወንድም

"በበለፀጉት ሃገራት ቴክኖሎጂን ምቾት ለመፍጠርና ነገሮችን ለማቅለል ነው የሚጠቀሙበት። በኢትዮጵያ ግን የግድ አስፈላጊ ስለሆነ ነው" ትላለች በአይኮግስ ላብስ የቴክኖሎጂ አስተማሪዋ ቤቴልሄም ደሴ።

ኢትዮጵያ ምጣኔ ሃብታዊ እድገት ቢኖራትም አሁንም በዓለም ዝቅተኛ የነፍስ ወከፍ ገቢ ካላቸው ሃገራት ተርታ የምትሰለፍ ነች። አብዛኛው የሃገሪቱ ዜጋም ሕይወቱ ከኋላ ቀር የእርሻ ሥራ ጋር የተሳሰረ ነው። አሁን ወጣቶች ይህን ችግር በቴክኖሎጅ ለመቀየር እየሠሩ ነው።

"ትልልቅ ሃሳቦች ለችግሮች መፍትሄ ናቸው" የሚሉት የብሉ ሙን መሥራች እሌኒ ገብረ መድህን "ያለን ማንኛውም ነገር ሁሉ በችግር የተሞላ ነው"ይላሉ።

ኤምፔሳ የተባለውን የኬንያ የመገበያያ ዘዴ በምሳሌነት ያነሱት ዶክተር እሌኒ የግብይት ሂደቱን በተለየ መልኩ ለመለወጥና ምጣኔ ሃብቱን ለማሳደግ ከፍተኛ እገዛ አድርጓል ይላሉ።

ይህን ለማድረግ ኢትዮጵያ ውስጥ የባንኮች አሠራር የዘመነ ስላልሆነ ኢኮኖሚውን ማነቃቃት አልተቻለም ብለዋል። በተለይ ግብርና፣ ትምህርት እና ጤና ይህ ዓይነት ቴክኖሎጂ በእጅጉ ያስፈልጋቸዋል ባይ ናቸው።

ሌላኛው በቴክኖሎጂ ፈጠራ ላይ የሚሠራው ማረቆስ ለማ የሞባይል ሶፍትዌር፣ የሶላር ኃይልና ማይክሮ ፋይናንስን በማቀናጀት የውሃ ቧንቧዎችን ለመሥራት የሚያስችል ቴክኖሎጂ ፈጥሯል። "ለአካባቢያዊ ችግር አካባቢያዊ መፍትሄ መስጠት ያስፈልጋል መፍትሄውን ከሌላ ከመኮረጅ ይልቅ" ይላሉ አቶ ማርቆስ።

ማርቆስ በ2003 ፍሎውየስ የተባለውን የቴክኖሎጅ ማበልፀጊያ ከጓደኞቻቸው ጋር ሲያቋቁሙ በአዲስ አበባ የመጀመሪያዎቹ ነበሩ። ነገር ግን በ10 ዓመት ጊዜ ውስጥ ከ100 በላይ ተመሳሳይ ሥራዎች ተቋቁመዋል።

ማርቆስ አንደሚለው ይህ የሆነው ደግሞ በዚያን ጊዜ የነበረው የአንድ ግለሰብ ኢንተርኔት የመጠቀም ባሕል ከ1% ወደ 15% ማደጉ፤ የስማርት ስልኮች ዋጋ መቀነስ የኢንተርኔት አገልግሎት እንዲያድግ ምክንያት ሆነዋል። እነዚህ ለውጦች መደረጋቸው ደግሞ ቴክኖሎጂው ላይ አዎንታዊ ተጽዕኖ እንዲኖር አድርጓል።

ማርቆስ ለማ

የፎቶው ባለመብት, Thomas Lewton

የምስሉ መግለጫ, ማርቆስ ለማ

"የሃገሪቱ ባሕላዊ እሴቶች በእራሳቸው አዲስ ነገር እንድታመጣ መንገድ ይከፍታሉ" የሚሉት አቶ ማርቆስ ለምሳሌ ሰዎች ዕቁብ ሲጥሉ ተሰባስበው በመቁጠርና ጊዜ በማጥፋት ሊጉላሉ ይችላሉ። አሁን ግን ዕቁብን በተንቀሳቃሽ ስልክ መተገበሪያ ማድረግ ተችሏል ብለዋል።

ሌላኛው የኮግ ላብሰ መስራች ጌትነት አሰፋ እንደሚለው "የኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ እድገት ያለጥገኝነት የሚያድግ ነው። የእነ ናይጀሪያና ኬንያ ቴክኖሎጂ በውጭ ባለሃብቶች የሚሳለጥ ነው። የኢትዮጵያ ግን ከእነ ችግሩም ቢሆን በኢትዮጵያውያን የሚሠራ ነው።"

ከጠቅላይ ሚንስትሩ ጋር ሶፊያ የተባለችው ሮቦት ስትገናኝም የተወሰኑ የአማርኛ ቃላትን እንድትናገር ያደረጋት አሰፋ ጌትነት ጠቅላይ ሚንስትሩ ለቴክኖሎጂው ዘርፍ እገዛ እንደሚያደርጉላቸውም ተስፋ አድርጓል።

አሁን ላይ ማርቆስ፣ እሌኒና ሌሎችም በአንድነት ሆነው ቴክኖሎጂውን ከማበልፀግ ባሻገር የማሳያ ቦታዎችን በማዘጋጀት፣ ኔትዎርክ በመዘርጋትና ዕድሎችን በማመቻቸት እየሠሩ ነው። "አሁን ሁሉንም ያካተተ ሥራ እየሠራን ነው" ብለዋል ዶክተር እሌኒ።

ኢትዮጵያ እንደሃገር ባለፉት ዓመታት የዩኒቨርሲቲዎችን ቁጥር ወደ 40 ከፍ አድርጋለች። 70% የሚሆኑት ወደእነዚህ ተቋማት የሚላኩ ተማሪዎችም የሳይንስና የምህንድስና ትምህርት እንዲማሩ ተደርጓል።

በመሆኑም ይህን ዕድል ለመጠቀም በእነዚህ ተቋማት የሚማሩ ተማሪዎችን ለመድረስ የሚያስችልና ስሜታቸውንና የፈጠራ ክህሎታቸውን የሚያዳብሩበት ቦታ የማመቻቸት ሥራ እንሠራለን ብለዋል ዶክተር እሌኒ።