በኢትዮ-ኤርትራ ድንበር ንግድ ተጧጡፏል

በኢትዮጵያ እና በኤርትራ መካከል ለ20 ዓመታት ያህል ዘልቆ የነበረው ሰላምም ሆነ ጦርነት ያልነበረበት ፍጥጫ ከወራት በፊት በተደረሰው የሰላም ስምምነት መቋጫውን አግኝቷል።

ከአዲስ አበባ ወደ አሥመራ የሚደረገው በረራ የቀጠለ ቢሆንም፤ ቪዛ እና የቀረጥ ጉዳዮችን መልክ ለማስያዝ በሚል ምክንያት በእግር እና በመኪና ድንበር ማቋረጥ ተከልክሎ ቆይቷል።

ይሁን እንጂ የድንበር ከተሞች ላይ የሚገኙ ነዋሪዎችን በድንበር ከተሞቹ ላይ ንግዳቸውን ከማጧጧፍ ያገዳቸው የለም።

ለሱዳን ቅርብ የሆነው ሁመራ-ኦመሃጀር ድንበር በቅርቡ መከፈቱ ይታወሳል። ድንበሩ መከፈቱን ተከትሎም በድንበር አቅራቢያ ከፍተኛ የሆነ የትራፊክ ፍሰት እየተስተዋለ ነው።

በሁመራ ገንዘብ መንዛሪዎች ከመቼውም በላይ ንግድ ደርቶላቸዋል። አንድ ዶላር የሚመነዘረው በ15 ናቅፋ ገደማ ሲሆን፤ አንድ ዶላር ደግሞ 28 ብር ገደማ ይመነዘራል። በአካባቢውም ብር ወደ ናቅፋ የሚመነዝሩ ነጋዴዎች ይገኛሉ።

በምስሉ ላይ የሚታየውን አልጋ የሚሰሩ እና የሚሸጡ ሰዎች የደንበኞቻቸው ቁጥር እየጨመረ መሆኑን ይናገራሉ። አካባቢው እጅጉን ሞቃታማ ከመሆኑ የተነሳ ሰዎች በእነዚህ አልጋዎች ላይ ከቤት ውጪ ይተኛሉ።

በሁለቱ ሀገራት መካከል ተከስቶ በነበረው ግጭት የአንድ ቤተሰብ አባላት በሁለት ሀገራት ተከፍለው ለዓመታት ሳይገናኙ ቆይተዋል። የሰላም ስምምነት ላይ ከተደረሰ በኋላ ለዓመታት ተለያይተው የቆዩ ሰዎች እየተገናኙ ነው።

የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት መጀመሩን ተከትሎ ቤት ንብረታቸውን ጥለው ሀገር ጥለው የወጡ በርካቶች ናቸው።

ከእነዚህ መካከል ከዚህ በታች የሚታዩት ኤርትራውያን ይገኙበታል። እኚህ ሁለት ሰዎች እንደሚሉት፤ ከሁለት አሰርት ዓመታት በፊት ጥለው የሄዱትን ንብረት ይገባኛል የሚል ጥያቄ ሊያነሱ ሁመራ ተገኝተዋል።